[FrontPage Image Map Component]

የሙስና መከላከልና ምርምር መምሪያ አግባብነት ካላቸው አካላት ጋር በመተባበር የሙስና ወንጀልና ብልሹ አሠራርን ለመከላከል ከኮሚሽኑ ዓላማ አስፈፃሚ መምሪያዎች አንዱ ሆኖ የተደራጀ ነው፡፡ 

መምሪያው የተሰጡትን ኃላፊነቶች ለመወጣት ይችል ዘንድ 28 ባለሙያዎችንና የሥራ ኃላፊዎችን በመያዝ በሦስት ዲቪዥኖች ተደራጅቶ ይገኛል፡፡ ዲቪዥኖቹም፡-

የሙስና መከላከልና ምርምር ዲቪዥን አንድ
የሙስና መከላከልና ምርምር ዲቪዥን ሁለት
የሥነምግባር ምርምር ማዕከል ዲቪዥን ሦስት ሲሆኑ፣ በሰው ኃይል በኩል ከላይ ከተጠቀሱት ውስጥ አንድ የመምሪያ ዳይሬክተር፣ ሦስት ምክትል ዳይሬክተሮችና ሁለት ፀሐፊዎች ይገኙባቸዋል፡፡

መምሪያው በአዋጅ ቁጥር 433/97 ኮሚሽኑ ከተሰጡት ሥልጣንና ተግባራት መካከል ሙስናንና ብልሹ አሠራርን ከመከላከል ጋር የተያያዙት  ሥልጣንና ተግባራት በቀጥታ ይመለከቱታል፡፡ እነዚህም ሥልጣንና ተግባራት ጠቅለል ብለው ሲታዩ፡-

የአሠራር ሥርዓት ጥናቶችን ማካሄድ፣
የምርመራ ሥራና የማስፈፀሚያ ደንብና መመሪያ በማዘጋጀት ስር ሊጠቃለሉ የሚችሉ ናቸው፡፡

መምሪያው  እስካሁን ያከናወናቸው ዋና ዋና ተግባራት

መምሪያው ከላይ የተገለፀውን አደረጃጀትና የሰው ኃይል በመያዝ የሚከተሉትን ተግባራት በማከናወን ላይ ይገኛል፡፡ 

የአሠራር ሥርዓት ጥናቶችና የምርምር ሥራ

የሙስና መከላከልና ምርምር መምሪያ የመንግሥት መ/ቤቶችና የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን ማዕከል በማድረግ የአሠራር ሥርዓት ጥናቶች ሲያካሂድ ቆይቷል፡፡ ከዚህ አንፃር እስከአሁን ድረስ በመምሪያው 19 የሚደርሱ መንግሥታዊ ተቋማት የአሠራር ሥርዓቶች ተጠንተው የተጠናቀቁ ሲሆን 5 መንግሥታዊ ተቋማት ደግሞ በመጠናት ላይ  ይገኛሉ፡፡ ከዚህ ጐን ለጐን መምሪያው ከሙስና እና ከሥነምግባር ጋር የተያያዙ የምርምር ጥናቶችንም ያካሂዳል፡፡

የምርምር ሥራ፣ የማስፈፀሚያ ደንብና መመሪያ ዝግጅት

ከሙስና እና ከሥነምግባር ጋር የተያያዙ የምርምር ጥናቶችን ማካሄድና የኮሚሽኑን ማቋቋሚያ ሕግ ለማስፈፀም የሚያግዙ ደንቦችና መመሪያዎችን ማዘጋጀትና ለሚመለከታቸወ አካላት አስቀርቦ እንዲፀድቅ ክትትል የማድረግ ሥራዎችን ማከናወን ከመምሪያው የሚጠበቅ ሁለተኛው ዐቢይ የሥራ ዘርፍ ነው፡፡ 

መምሪያው የአሠራር ሥርዓት ጥናት እና የምርምር ስራዎችን ለመፈፀም የሚከተላቸው ስልቶች 

በመንግሥት መ/ቤቶች እና በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ውስጥ ለሙስና እና ለብልሹ አሠራር የተጋለጡና መጋለጥ የሚችሉ የአሠራር ሥርዓቶችን በማጥናት እንዲሻሻሉ የማማከርና የማሳሰብ አገልግሎቶችን ቁጥራቸው ከ36ዐ ለሚበልጡ የመንግሥት መ/ቤቶችና የልማት ድርጅቶች በአንድ ጊዜ ለማከናወን ኮሚሽኑ አሁን ባለው ውስን የሰው ኃይልና አደረጃጀት አዳጋች ነው፡፡ በዚህ ምክንያት የግዴታ ቅድሚያ ተሰጥቷቸው የሚጠኑ ተቋማትን መምረጥ አስፈላጊ ነው፡፡ 

በመሆኑም እስከቅርብ ጊዜ ድረስ የመንግሥት ተቋማትን የአሠራር ሥርዓት ጥናት ለማካሄድ ቅድሚያ ተሰጥቷቸው የሚጠኑ መንግሥታዊ ተቋማትን ለመምረጥ የሚያስችሉ መስፈርቶች የያዘ የመምረጫ መመሪያ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ ሲሆን ቆይቷል፡፡ 

ከሕዳር 1997 ዓ.. ጀምሮ ደግሞ ለሙስና እና ለብልሹ አሠራር ከተጋለጡ የመንግሥት መ/ቤቶችና የልማት ድርጅቶች መካከል ቅድሚያ ተሰጥቷቸው የአሠራር ሥርዓት ጥናት የሚካሄድባቸውን ተቋማት ለመለየትና ደረጃ ለማውጣት የሚያስችል መመሪያ ወጥቶ ተግባራዊ ሆኗል፡፡ 

መምሪያው የአሠራር ሥርዓቶቻቸው የሚጠኑ ተቋማትን ለመምረጥ ከሚጠቀምበት መመሪያ በተጨማሪ የተመረጡት ተቋማት የአሠራር ሥርዓት ምን ላይ ተጀምሮ የት መጠናቀቅ እንዳለበት የሚያመላክት የአሠራር ሥርዓት የአፈፃፀም መመሪያ አዘጋጅቶ ተፈፃሚ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

መምሪያው ይህን የአሠራር ሥርዓት ጥናት መመሪያ ተከትሎ ሥራን ለማቀላጠፍና የበርካታ መንግሥታዊ ተቋማትን የአፈፃፀም ብቃትና የአሠራር ሥርዓቶች በተፋጠነ ሁኔታ ለማጥናት የሚያስችለው አዲስ መመሪያ አዘጋጅቷል፡፡ ይህ አዲስ መመሪያ አምስት ስልቶችን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ነው፡፡ 

እነዚህም፡-

1.      በመንግሥት መ/ቤቶችና የልማት ድርጅቶች ያሉና የተቋቋሙ የሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች የየመ/ቤቶቻቸው ሥራዎችና የአሠራር ሥርዓቶች ለሙስናና ለብልሹ አሠራር የተጋለጡ እንዳይሆኑ የአሠራር ሥርዓት ጥናት እንዲያካሂዱ ሁኔታዎችን ማመቻቸትና በጥናት ሂደቱ ላይ በየደረጃው የሚፈለገውን ድጋፍ መስጠትና መከታተል፣

2.      ከልማትና የዲሞክራሲ ግንባታ ስትራቴጂ አንፃር ቁልፍ ሚና የሚጫወቱና ለሙስናና ለብልሹ አሠራር በመጋለጣቸው በአጠቃላይ በተያዘው የልማትና የዲሞክራሲ ጐዳና ላይ ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርሱ በሚችሉ ተቋማት ላይ ከሌሎች ተቋማት የበለጠ ትኩረት በመስጠትና የመምሪያውን ባልደረቦች በእነዚህ ተቋማት በቋሚነት ወይም በተወሰነ ጊዜ በዙር መድቦ ለሙስናና ለብልሹ አሠራር የተጋለጡ አሠራሮች እንዲሻሻሉ በየጊዜው መፈተሽና ተግባራዊነቱን በቋሚነት መከታተል፡፡

3.      በመምሪያው በተዘጋጀው የአሠራር ሥርዓቶቻቸውን ለማጥናት መምረጫ መመሪያ መሠረት የተቋማቱን ሥራዎችና የአሠራር ስርዓቶች መፈተሽ፣ ማጥናት፣ የመፍትሄ ሃሳብ መጠቆም፣

4.      በተለያየ መልኩ/ ከጥቆማ፣ ከሚዲያ፣ ከምርመራ መምሪያ ከበላይ አካል ወዘተ/ ለመምሪያው ከሚቀርቡ (specific) ጉዳዮች መካከል ቅድሚያ የሚሰጣቸውን በመለየት የአሠራር ሥርዓት ጥናት ማድረግና እንዲሻሻሉ የሚያስችል ምክር መስጠት፣

5.      የአንድ መ/ቤትን አሠራር እንዲሻሻል ግቡ ያደረገ ሳይሆን አጠቃላይ ጥናት የሚያስፈልጋቸውን ሥራዎች/ ለምሳሌ የግዥ አፈፃፀም፣ የንብረት አስተዳደር፣ የፋይናንስ አስተዳደር ወዘተ...) ከሙስና አንፃር ያላቸውን ተጋላጭነት በመለየትና በማጥናት ተቀባይነት ያለው መመሪያ ማዘጋጀትና ለተጠቃሚ ክፍሎች አሠራራቸውን እንዲፈትሹት ማሰራጨት፣ ውጤቱን በሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች አማካኝነት መከታተል ናቸው፡፡ 

የተሻሻለው ይህ የአሠራር ሥርዓት ጥናት መመሪያ ከላይ ከተገለፁትና የመመሪያው አካል ከሆኑት ጉዳዮች በተጨማሪ የድህረ አሠራር ሥርዓት ጥናት አፈፃፀም ክትትል ሥራ የት ተጀምሮ እንዴት ተከናውኖ በምን ላይ እንደሚጠናቀቅ የሚያመላክት አሠራርን ዝርዝር ይዞ ይገኛል፡፡