የአስተዳደርና ፋይናንስ መምሪያ

 የአስተዳደርና ፋይናንስ መምሪያ በዳይሬክተር የሚመራ ሲሆን በውስጡም የፋይናንስ ዩኒት፣ የሰው ኃይልና ስልጠና ዩኒት፣ የንብረት አስትዳደርና ጠቅላላ አገልግሎት ዩኒት እና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዩኒትን ይይዛል፡፡ መምሪያው ከዳይሬክተር በተጨማሪ ምክትል ዳይሬክተር አለው፡፡ ምክትል ዳይሬክተሩም በዋነኛነት የንብረት አስተዳደርና ጠቅላላ አገልግሎት ዩኒትን በበላይነት ይመራል፡፡ መምሪያው በአራቱም ዩኒቶች ወደ ሰባ የሚጠጋ የሰው ኃይል አለው፡፡

 እያንዳንዱ ዩኒት በዋነኛነት የሚያከናውነውን ተግባር ለመዘርዘር ያህል የመምሪያው የፋይናንስ ዩኒት በተለይ ከፋይናንስ አስተዳደርና ከበጀት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ያደራጃል በዚህ መሠረት የኮሚሽኑን የተለያዩ መሣሪያዎችና አገልግሎቶች በጀት በማዘጋጀት የኮሚሽኑን አጠቃላይ የገንዘብ አጠቃቀምና አያያዝ ይቆጣጠራል፡፡

 የሰው ኃይልና ስልጠና ዩኒት የኮሚሽኑን ሠራተኞች አስተዳደር ደንብ በመከተል ለኮሚሽኑ የሚያስፈልጉ ሠራተኞችን በቅጥር፣ በዝውውርና በእድገት እንዲሟሉ ያደርጋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የኮሚሽኑ ሠራተኞች ተገቢውን ሥልጠና እንዲያገኙ በየጊዜው ክትትል በማድረግ የሚያስፈፅም ሲሆን በተጨማሪም የሠራተኞችን የጡረታ፣ የሥራ መልቀቂያ፣ የፈቃድ እና ሌሎች ጉዳዮችን ያስፈፅማል፡፡

 የንብረት አስተዳደርና ጠቅላላ አገልግሎት ዩኒት ደግሞ ለኮሚሽኑ አስፈላጊ የሆኑ ቋሚና አላቂ ዕቃዎችንና አገልግሎቶችን በመግዛት ያሠራጫል፣ ያስተዳድራል፣ የጥገና ጉዳዮችንም ተከታትሎ ያስፈፅማል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የኮሚሽኑን ተሽከርካሪዎች የማስተዳደር፣ የማሰማራት የማስጠገን እና የኢንሹራንስ ጉዳዮችን የመከታተል ኃላፊነት የተሰጠው ለዚህ ዩኒት ነው፡፡ የኮሚሽኑን ሕንፃ የማስተዳደር፣ ልዩ ልዩ ጥገናዎችን የማስፈፀም፣ የአገልግሎት ክፍያዎችን የመፍቀድ እና ሌሎች ተመሳሳይ ጉዳዮችን ማከናወን የዚህ ዩኒት የሥራ ድርሻ ነው፡፡

 የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዩኒትም ተጠሪነቱ ለአስተዳደርና ፋይናንስ መምሪያ ሲሆን በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ ለኮሚሽኑ የሚያስፈልገውን የቴክኒክ ድጋፍ የሚያከናውነው ይህ የሥራ ክፍል ነው፡፡

 

 የኦዲት አገልግሎት

የውስጥ ኦዲት አገልግሎት ተጠሪነቱ ለፌደራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ሲሆን አገልግሎቱ በሁለት የሰው ኃይል ማለትም በአንድ የኦዲት አገልግሎት ኃላፊ እና በአንድ ኦዲተር የተደራጀ ነው፡፡ 

የኦዲት አገልግሎቱ የኮሚሽኑን  የፋይናንስ መረጃዎችንና መግለጫዎችን ትክክለኛነት በመመርመርና የመምሪያዎችን፣ የአገልግሎቶችንና ልዩ ልዩ የሥራ ክፍሎችን የሥራ ክንውን በመገምገም የኦዲት ሪፖርት ማቅረብ ኃላፊነት የተሰጠው አካል ሆኖ የኦዲት ሪፖርቱንም የሚያቀርበው በቀጥታ ለኮሚሽነሩ ነው፡፡  

አገልግሎቱ ከሚያከናውናቸው ዝርዝር ተግባራት መካከል፡-

የፋይናንስ መረጃዎችንና መገለጫዎችን ትክክለኛነት በመመርመር መረጃዎቹ የኮሚሽኑን ተጨባጭ ሁኔታ በትክክል ማሳየት አለማሳየታቸውን በማየት የኦዲት አስተያየት ማቅረብ፣
መምሪያዎችና ልዩ ልዩ የሥራ ክፍሎች ያቀዱትን ሥራ ማከናወናቸውን መገምገም፣
በቂና አስተማማኝ የፋይናንስ የውስጥ ቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋቱን በመገምገም የማሻሻያ ሃሳቦችን ማቅረብ፣
መምሪያዎች፣ አገልግሎቶችና ልዩ ልዩ የሥራ ክፍሎች ኮሚሽኑ ያለውን ሃብትና ገንዘብ በትክክል ለታለመለት ዓላማ ማዋላቸውን ለማረጋገጥ የክዋኔ ኦዲት ማካሄድ፣
መሻሻል በሚገባቸው የኮሚሽኑ የገንዘብ አስተዳደር አሰራሮች ላይ የማሻሻያ አስተያየት የማቅረብ፣
ጥሬ ገንዘብና ሰነዶች በተለይም ቼኮች፣ የቼክ ጉራጆች፣ የገንዘብ መሰብሰቢያ ደረሰኞችና ማስረጃዎች በአግባቡ መጠበቃቸውን መከታተል፣ የክፍያ ሰነዶች የሂሳብ ስሌት ትክክለኛ መሆኑን ማረጋገጥ፣  

እንዲሁም ሌሎች ተመሳሳይ ተግባራትን ማከናወን ለአገልግሎቱ የተሰጡ ኃላፊነቶች ናቸው፡፡

 የሙስና ወንጀል ምርመራ መምሪያ  

መምሪያው በመንግሥት መ/ቤቶች ወይም በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ወይም የፌደራል መንግሥቱ ለክልሎች ከሚሰጠው ድጐማ ጋር በተያያዘ በክልል መ/ቤቶች በወንጀል ሕግ እና በሌሎች ሕጐች ውስጥ የተመለከቱት የሙስና ወንጀሎች በመንግሥት ሠራተኞች ወይም ባለሥልጣኖች ወይም በሌሎች ሰዎች ስለመፈፀማቸው ጥቆማ ሲደርሰው ወይም በቂ ጥርጣሬ ሲኖረው የመመርመር  ወይም እንዲመረመር የማድረግ ተግባርና ኃላፊነት አለው፡፡ ከዚህ አንፃር የመምሪያው ዋና ተግባር የተጠረጠሩ የሙስና ወንጀሎችን እና የሥነምግባር ጥሰቶችን በማጣራት ጥፋተኞች ክስ እንዲመሰረትባቸው የምርመራውን ውጤት ለዐቃቤ ሕግ መምሪያ ማስተላለፍ ነው፡፡ 

በመሆኑም መምሪያው ከተለያዩ የሕብረተሰቡ ክፍሎች የሚደርሱትንና በሙስና ወንጀል እና በሥነምግባር መተላለፍ ዙሪያ የሚያተኩሩ ጥቆማዎችን በአካል፣ በስልክ ወይም በደብዳቤ በፋክስ እና በኢሜል አማካኝነት በመቀበል እንደችግሩ ይዘትና ስፋት ጥቆማው በቅደም ተከተል የሚደራጅበትንና ለምርመራ ዝግጁ የሚሆንበትን አሠራር ተግባራዊ ያደርጋል፡፡ 

ከዚህ በተጨማሪ መምሪያው የተጠርጣሪዎች ሀብት በፍርድ ቤት አማካኝነት እንዳይንቀሳቀስ በማስወሰን ተጠራጣሪዎቹ ጥፋተኝነታቸው ከተረጋገጠ ፍርድ ቤት በሚወስነው መሠረት የታገደው ንብረት ለፍርድ ማስፈፀሚያ እንዲውል ሊያደርግ ይችላል፡፡ 

ከሙስና ወንጀል ምርመራ መምሪያ ባለሙያዎች መካከል አንድን የተጠረጠረ የሙስና ወንጀል ጉዳይ እንዲመረምር የተመደበ ሠራተኛ ለምርመራ ሂደቱ ጠቃሚነት አለው ተብሎ እስከታመነበት ድረስ ከማንኛውም ድርጅት ወይም ግለሰብ መረጃ የማግኘት መብት አለው፡፡ ከዚህ መረዳት የሚቻለው ምርመራቸው በሂደት ላይ የሚገኙ ተጠርጣሪ የሙስና ወንጀሎችን ጉዳይ በተመለከተ መረጃ እንዲሰጥ የሚጠየቅ ማንኛውም አካል በተጠየቀው ጉዳይ ላይ መረጃ ለመስጠት ትብብር ሊያሳይ የሚገባው መሆኑን ነው፡፡ 

የሙስና ወንጀል ምርመራ መምሪያ ዳይሬክተር በሙስና የተጠረጠረን ግለሰብ ወይም ጉዳይ በምርመራ ላይ የሚገኝን ተጠርጣሪ በቁጥጥር ስር እንዲውል የሚያስገድድ አሳማኝ ምክንያት ካለው ከ48 ሰዓት ላልበለጠ ጊዜ በቁጥጥር ስር እንዲውል ትዕዛዝ የመስጠት ስልጣን አለው፡፡ ይህም ሲሆን ጉዳዩን በቅድሚያ ለሥነ ምግባርና ለፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አሳውቆ ስምምነት ማግኘት ይኖርበታል፡፡ 

በሌላ ወገን ደግሞ ማንኛውም የመንግሥት ተቋምም ሆነ ግለሰብ ከባድ የሥነምግባር መጣስን ጨምሮ  የሙስና ወንጀል ለመፈፀሙ ጥርጣሬ ሲኖረው ጉዳዩን ለኮሚሽኑ እንዲጠቁም ይጠበቃል፡፡ 

የተወሰኑ የመምሪያው ተግባራት እንዳስፈላጊነቱ በሚስጥር የሚጠበቁ ናቸው፡፡ ለምሳሌ በአንድ መንግሥታዊ ተቋም የሙስና ወንጀል ለመፈፀሙ ጥቆማ ለማቅረብ ወደ ኮሚሽኑ የሚመጡ የሕብረተሰብ ክፍሎች ማንነት በሚስጥር ሊጠበቅላቸው ይገባል፡፡ በተጨማሪም በጅምር የምርመራ ደረጃ ላይ የሚገኝ ጉዳይ በወንጀሉ ተጠያቂ አካላት እንዳይጠፉና ተፈላጊ መረጃዎቹም እንዳይሰወሩ ለማድረግ በሚስጥር ተጠብቆ መቆየቱ ይታመናል፡፡ ሆኖም ግን የሙስና ወንጀልን የማጣራት ሂደት በሚስጢር ተጠብቆ የሚቆየው ተጠርጣው በቁጥጥር ስር እስኪውል ድረስ ብቻ ነው፡፡ 

መምሪያው በጥቆማ የሚቀርቡለትን የተጠረጠሩ የሙስና ወንጀሎች ጉዳይ አንዱን ከሌላው ሳያበላልጥ ለሁሉም እኩል ትኩረት ሰጥቶ ምርመራ ሥራውን ያካሂዳል ምክንያቱም በጥቆማ አቀራረብ ላይ ዝቅተኛ የሙስና ወንጀል ጉዳይ መስለው የሚታዩ ጉዳዮች በምርመራ ሂደት ከፍተኛ የሙስና ወንጀል ያካተቱ ጉዳዮች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ በሌላ ወገን ማንኛውም የሕብረተሰብ ክፍል በፀረ-ሙስና ዘመቻው ላይ የሚያሳየው ተሳትፎ የተጠናከረ እንዲሆን ከተፈለገ ሁሉም ዜጋ ለኮሚሽኑ በጥቆማ የሚያቀርባቸው የሙስና ጉዳዮች ተገቢው ትኩረት ተሰጥቷቸው መጣራት ስለሚገባቸው ነው፡፡

ይህም በአነስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ የሙስና ወንጀሎች ሳይቀሩ በኮሚሽኑ ትኩረት ተሰጥቷቸው ተገቢው ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድባቸው መደረጉ ሙስናን ሊሸከም የማይችል  ሕብረተሰብ  ለመገንባት ለሚደረገው ጥረት አስተዋፅኦ ስለሚኖረው የትኛውም የሙስና ወንጀል ከሕዝብ ዕይታ ተሰውሮ ብዙ እንዳይቆይ ያደርጋል፡፡

 የሙስና መከላከልና ምርምር መምሪያ

 የሙስና መከላከልና ምርምር መምሪያ አግባብነት ካላቸው አካላት ጋር በመተባበር የሙስና ወንጀልና ብልሹ አሠራርን ለመከላከል ከኮሚሽኑ ዓላማ አስፈፃሚ መምሪያዎች አንዱ ሆኖ የተደራጀ ነው፡፡ 

መምሪያው የተሰጡትን ኃላፊነቶች ለመወጣት ይችል ዘንድ 28 ባለሙያዎችንና የሥራ ኃላፊዎችን በመያዝ በሦስት ዲቪዥኖች ተደራጅቶ ይገኛል፡፡ ዲቪዥኖቹም፡-

የሙስና መከላከልና ምርምር ዲቪዥን አንድ
የሙስና መከላከልና ምርምር ዲቪዥን ሁለት
የሥነምግባር ምርምር ማዕከል ዲቪዥን ሦስት ሲሆኑ፣ በሰው ኃይል በኩል ከላይ ከተጠቀሱት ውስጥ አንድ የመምሪያ ዳይሬክተር፣ ሦስት ምክትል ዳይሬክተሮችና ሁለት ፀሐፊዎች ይገኙባቸዋል፡፡

መምሪያው በአዋ