ከባድ የዕምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል የፈጸመ ግለሰብ ተፈረደበት

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከባድ የዕምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል ፈጽሟል በማለት ክስ በመሰረተበት አብርሃም አሰግዶም ላይ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ጥር 17 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት የ12 ዓመት ጽኑ እስራትና የገንዘብ ቅጣት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

ተከሳሹ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን የደቡብ አዲስ አበባ ሪጅን የዕቃ ግምጃ ቤት ዋና ኃላፊ ( Supply and Logistic Performer) ሆኖ በሚሰራበት ወቅት ከታህሳስ 10 እስከ ጥር 13 ቀን 2003 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ በሥራ ምክንያት በእጁ የገቡ የኮርፖሬሽኑን ንብረቶች አጉድሎ በመገኘቱ ክስ እንደተመሰረተበት ታውቋል፡፡

ተከሳሹ ያጎደለው የኮርፖሬሽኑ ንብረቶች የዋጋ ግምት ብር 605,011.99 (ስድስት መቶ አምስት ሺህ አስራ አንድ ብር ከዘጠና ዘጠኝ ሳንቲም) ሲሆን ግለሰቡ ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለማግኘት በማሰብ ያጎደላቸውን ንብረቶች ለራሱ ጥቅም ያዋለ እና ከባድ የዕምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል የፈፀመ መሆኑን ክሱ ያመለክታል፡፡

ግለሰቡም በክስ ሂደቱ ኮሚሽኑ ያቀረበበትን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች መከላከል ባለመቻሉ በ12 ዓመት ጽኑ እስራትና በብር 35,000 (ሰላሳ አምስት ሺህ) እንዲቀጣ ፍርድ ቤቱ ጥር 17 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላልፏል፡፡  

   

 

በሙስና ወንጀል ክስ የተመሰረተባቸው 21 ተከሳሾች የእስራትና የገንዘብ ቅጣት ተወሰነባቸው

የፌዴራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከአንድ መቶ ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የመንግስት መሬት በሕገወጥ መንገድ ከመያዝ ጋር በተያያዘ ክስ የመሰረተባቸው 21 ተከሳሾች እስከ አስራ አንድ ዓመት በሚደርስ ፅኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ጥር 15 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

የክስ ውሳኔው የተላለፈባቸው ተከሳሾች 2ኛ ተከሳሽ አባይ ለገሰ፣ 3ኛ ተከሳሽ ባልቻ ኃ/ማሪያም፣ 4ኛ ተከሳሽ ተሾመ ታደገ፣ 5ኛ ተከሳሽ መልካሙ ፈንታዬ፣ 6ኛ ተከሳሽ ነጋሽ መለሰ፣ 7ኛ ተከሳሽ ገስጥ ግርማ፣ 8ኛ ተከሳሽ በኃይሉ አንዳርጌ፣ 9ኛ ተከሳሽ የምስራች አሰፋ፣ 10ኛ ተከሳሽ ታጠቅ ታደሰ፣ 11ኛ ተከሳሽ ሰለሞን መልሴ፣ 12ኛ ተከሳሽ ካሳሁን ለማ፣ 13ኛ ተከሳሽ ሙራድ በድሩ፣ 14ኛ ተከሳሽ ሞላ ወልቀባ፣ 15ኛ ተከሳሽ መሐመድ ሐሰን፣ 16ኛ ተከሳሽ ግርማቸው ከበደ፣ 17ኛ ተከሳሽ ሀብቱ በየነ፣ 18ኛ ተከሳሽ ሙባረክ በድር፣ 19ኛ ተከሳሽ ኢዮብ ኃይሉ፣ 20ኛ ተከሳሽ አብዱ ረዲ፣ 21ኛ ተከሳሽ ፀጋዘአብ ኃይለሚካኤል፣ 22ኛ ተከሳሽ ገብረ ማርያም ፍትዊ መሆናቸውን የኮሚሽኑ አቃቤ ሕግ ገልጿል፡፡

በተከሳሾቹ ላይ የተመሰረተው ክስ እንዳመለከተው ተከሳሾቹ ከ1991 ዓ.ም. ወዲህ በሕገወጥ መንገድ የተቋቋመን ማህበር ቀደም ሲል በ1981 ዓ.ም በደርግ ጊዜ በሕጋዊ መንገድ የተቋቋመ ማህበር በማስመሰል በራሳቸው፣ በቤተሰቦቻቸው፣ በዘመዶቻቸው እና በሌሎች ግለሰቦች ስም “ታቦር” የተባለ ሕገወጥ የመኖሪያ ቤት ህብረት ሥራ ማህበር በሐሰት ፈጥረው አደራጅተዋል፡፡ በ1981 ዓ.ም በ24 አባላት የተቋቋመውንና በእንጥልጥል የቆየውን “ታቦር” የተባለ ማህበር ስያሜ ሰነዶችና ፋይል በሐሰት በመጠቀም የአባላቱን ቁጥርም ወደ 396 በማሳደግ በግልፅም ሆነ በስውር ራሳቸውን የማህበሩ አመራር ኮሚቴ አድርገው በየተራ እየተቀባበሉ በመሿሿም ፣ የመንግስትን የከተማ ቦታ በሕገወጥ መንገድ በወረራ በመያዝና መንግስት ለማህበሩ ቦታ አጥንቶ እንደመደበለት በማስመሰል በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር በመላ ሀሳባቸውና አድራጎታቸው በወንጀሉ ድርጊትና በሚሰጠው ውጤት ሙሉ ተካፋዮች በመሆን በመንግስት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስና ለራሳቸው ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለማግኘትም ሆነ ለሌላ ሰው ለማስገኘት በማሰብ የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል፡፡

በአጠቃላይ ተከሳሾቹ ቦታው የተገኘው መንግስታዊ ሰነዶችን በሐሰት አስመስሎ በማዘጋጀት፣ ወደ ሐሰት አስመስሎ በማዘጋጀት፣ ወደሀሰት በመለወጥና በመገልገል በግብርአበርነት በስልጣን ለአግባብ በገልገል በህገወጥ መንገድ በተደራጀ ማህበር ስም መሆኑን እና የቦታውን ህገወጥ አመጣጥ በመሰወር ሕጋዊ አስመስለው በመሸጥ፣ ወደ 3ኛ ወገን በማስተላለፍ እና የማህበሩ ተተኪ አባል እንደሆኑ አድርገው በመመዝገብ የማህበሩን መታወቂያ በመስጠት ለራሳቸው ህገወጥ የሆነ ጥቅም በማግኘታቸው ሁሉም ተከሳሾች በሙሉ እውቀታቸውና ፈቃዳቸው በሙስና ወንጀል የተገኘን ንብረት ሕጋዊ አስመስሎ በማቅረብና በወንጀሉ መርዳት የሙስና ወንጀል ተከሰዋል፡፡ በዚህም ብር 109‚836‚460/አንድ መቶ ዘጠኝ ሚሊዮን ስምንት መቶ ሰላሳ ስድስት ሺህ አራት መቶ ስልሳ ብር/ ግምት ያለው 63‚360 ካ.ሜ የሆነ የመንግስት መሬት ሕገወጥ በሆነ መንገድ እንዲያዝ ሆኗል፡፡

በመሆኑም ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃ መከላከል ባለመቻላቸው 2ኛ ተከሳሽ በ3ዓመት ከ6 ወር ፅኑ እስራትና በ2500ብር፤ 3ኛ፣4ኛ፣8ኛ፣10ኛ እና 20ኛ ተከሳሾች እያንዳንዳቸው በ8ዓመት ፅኑ እስራትና በ6ሺህ ብር፤ 5ኛ ተከሳሽ በ5 ዓመት ፅኑ እስራትና በ6ሺህ ብር፤ 6ኛ፣11ኛ፣12ኛ፣16ኛ፣19ኛ እና 22ኛ ተከሳሾች ደግሞ እያንዳንዳቸው በ5 ዓመት ፅኑ እስራትና በ1000 ብር፣ 7ኛ ተከሳሽ በ5 ዓመት ፅኑ እስራትና በ5000 ብር፣ 9ኛ ተከሳሽ በ9 ዓመት ፅኑ እስራትና በ6ሺህ ብር፣ 13ኛ ተከሳሽ በ7ዓመት ከ8 ወር ፅኑ እስራትና 3ሺህ ብር፣ 14ኛ ተከሳሽ በ11 ዓመት ፅኑ እስራትና በ10ሺህ ብር፣ 15ኛ ተከሳሽ በ4ዓመት ፅኑ እስራትና በ1000 ብር፣ 17ኛ ተከሳሽ በ7 ዓመት ከ8 ወር ፅኑ እስራትና በ8ሺህ ብር፣ 18ኛ ተከሳሽ በ7 ዓመት ከ8 ወር ፅኑ እስራትና በ3ሺህብር፣ 21ኛ ተከሳሽ በ6 ዓመት ከ6ወር ፅኑ እስራትና በ6 ሺህ ብር እንዲቀጡ ተወስኖባቸዋል፡፡ 

   

 

የፌዴራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የድሬዳዋ ቅርንጫፍ ፅ/ቤት በስድስት ወራት አበረታች ተግባራት አከናውኗል

የፌዴራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የድሬዳዋ ቅርንጫፍ ፅ/ቤት ባለፉት ስድስት ወራት ህብረተሰቡን በማስተማር፣ ሙስናን በመከላከል፣ በመመርመርና በመክሰስ አበረታች ተግባራትን ማከናወኑን አስታወቀ፡፡

ፅህፈት ቤቱ ከሐምሌ 1 ቀን 2003 ዓ.ም እስከ ታህሳስ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ካከናወናቸው ተግባራት መካከል ቀደም ሲል በምርመራ ላይ የነበሩትን እና በ6 ወራቱ ውስጥ አዲስ የቀረቡትን ጨምሮ 56 መዝገቦች ተመርምረው ለዐቃቤ ሕግ ለውሳኔ የቀረቡ ሲሆን 103 መዝገቦች ደግሞ ውሳኔ አግኝተዋል፡፡

ፅ/ቤቱ በፍርድ ቤት ክስ ከመሠረተባቸው ተከሳሾች መካከል 61ዱ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ የጥፋተኝነት ውሳኔ እንዲወሰንባቸው አድርጓል፡፡ በመሆኑም የፅ/ቤቱ የማስቀጣት አቅም በመዝገብ 75 በመቶ ሲሆን በተከሳሽ ደግሞ 79.2በመቶ መሆኑ ታውቋል፡፡

በተጨማሪም በሙስና የተገኘ ንብረትን ለመንግስት እንዲመለስ ማድረግን በተመለከተ ደግሞ ሶስት መኖሪያ ቤቶች፣ አንድ የመስክ መኪና(ላንድ ክሩዘር) እንዲሁም በባንክ የሚገኝ ብር 127‚290.80(መቶ ሃያ ሰባት ሺህ ሁለት መቶ ዘጠና) ብር እገዳ የተከናወነ መሆኑ ታውቋል፡፡

በስድስት ወራት 365 ለሚሆኑ ከተለያዩ ከቀበሌዎችና ሴክተር መስሪያ ቤቶች ለተውጣጡ የፋይናንስ ባለሙያዎችና ሠራተኞች እንዲሁም 40 ለሚሆኑ ከተለያዩ ት/ቤቶች ለተውጣጡ የሥነምግባርና የሥነዜጋ ክበብ አባላትና አመራሮች በስነምግባር እና በሙስና ወንጀል ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠናዎች መሰጠታቸውን ፅ/ቤቱ አስታውቋል፡፡

   

 

የሙስና ወንጀል የፈጸመ ግለሰብ በፅኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ ተወሰነበት

የፌዴራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በከባድ አታላይነትና ሰነዶችን ወደ ሀሰት በመለወጥ የሙስና ወንጀል ክስ የመሰረተበት ግለሰብ በ7ዓመት ከ9 ወር ፅኑ እስራትና በ17 ሺህ ብር መቀጮ እንዲቀጣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ጥር 10 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

ተከሳሽ ቴዎድሮስ አምጣቸው የማይገባ ብልጽግና ለራሱ ለማግኘት ወይም ለሌላ ሰው ለማስገኘት አስቦ በዕድገት የጎልማሶች አዳሪ ትምህርት ቤት በሂሳብ ክፍል ኃላፊነት ሲሰራ ትምህርት ቤቱ ለተለያየ የስራ ክፍል ሰራተኞች የደንብ ልብስ ለመግዛት ለአቅራቢዎች ባደረገው ጥሪ መሰረት በውድድሩ አሸናፊ ለሆነው ለወ/ሮ ፀሀይወርቅ ሲማ ድርጅት የሚከፈለውን ገንዘብ በወጪ ማዘዣ ደረሰኝ 10‚188.21ብር (አስር ሺህ አንድ መቶ ሰማንያ ስምንት ብር) ወ/ሮ ፀሀይወርቅ ሲማ ክፍያውን ለእርሱ እንዳስተላለፉለት በማስመሰል ኢንዶርስ (endorse) ማድረጉን የምርመራ መዝገቡ አስታውቋል፡፡

በመሆኑም ተከሳሹ መጋቢት 28 ቀን 2001 ዓ.ም ብሄራዊ ባንክ ቀርቦ ከመስሪያ ቤቱ  10‚188.21ብር (አስር ሺህ አንድ መቶ ሰማንያ ስምንት ብር ከሃያ አንድ ሳንቲም) ፈርሞ ወጪ በማድረግ ለግል ጥቅሙ በማዋሉ በፈጸመው የከባድ አታላይነት የሙስና ወንጀል መከሰሱን መዝገቡ ጠቁሟል፡፡በተከሳሹ ላይ የተመሰረተው 2ኛ ክስ እንደሚያመለክተው ደግሞ ለራሱ ወይም ለሌላ ሰው ተገቢ ያልሆነ መብት ወይም ጥቅም ለማግኘት ወይም ለማስገኘት ወይም በሌላ ሰው መብት ወይም ጥቅም ላይ ጉዳት ለማድረስ አስቦ ከላይ በ1ኛ ክስ ውስጥ የተጠቀሰውን ብር 10188.219(አስር ሺህ አንድ መቶ ሰማንያ ስምንት ብር ከሃያ አንድ ሳንቲም) ከባንኩ ፈርሞ ወጪ በማድረግ ለግል ጥቅሙ በማዋሉ በፈፀመው የንግድ ወይም ተላላፊ ዋስትና ሰነዶችን ወደ ሀሰት መለወጥና ማጥፋት ወንጀል ተከሷል፡፡

በመሆኑም ተከሳሹ የቀረበበትን የሰውና የሰነድ ማስረጃ መከላከል ባለመቻሉ ከላይ የተጠቀሰው የእስራትና የገንዘብ ቅጣት ተወስኖበታል፡፡ 

   

 

በሙስና ወንጀል ክስ የተመሰረተባቸው አራት ተከሳሾች ተፈረደባቸው

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የሙስና ወንጀል ፈጽመዋል በማለት ክስ የመሰረተባቸው አራት ተከሳሾች እስከ 5 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራትና እስከ ብር 5,500.00 በሚደርስ የገንዘብ መቀጫ እንዲቀጡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ጥር 16 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡  

ኮሚሽኑ በተከሳሾቹ ላይ የመሠረተው 1ኛ ክስ እንደሚያስረዳው የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ላንቻ ማዘዣ ጣቢያ አዛዥ የነበረው 1ኛ ተከሳሽ ም/ኮማንደር ግርማ ሰንበቶ እንዲሁም በግል ስራ የሚተዳደሩት 2ኛ ተከሳሽ ፍቃዱ ኦልጅራ፣ 3ኛ ተከሳሽ አብዱራዛቅ ዑመር፣ 5ኛ ተከሳሽ ዓለም ገብሬ በሙሉ ፈቃዳቸውና ዕውቀታቸው የወንጀል ተካፋይ በመሆን የማይገባ ጥቅም ለማግኘትና በሌላ ሰው መብት ላይ ጉዳት ለማድረስ በማሰብ የሙስና ወንጀል መፈጸማቸውን ይገልጻል፡፡

በዚህ መሠረት 2ኛ ተከሳሽ ፍቃዱ ኦልጅራ ታህሳስ 9 ቀን 2001 ዓ.ም  የግል ተበዳይ የሆነውን አቶ አለማየሁ እሸቱን “የሰጠሁህን ቼክ መልስልኝና በምትኩ ገንዘብ እሰጥሀለሁ” በማለት ባቀረበለት ጥያቄ መሠረት አዲስ ከተማ ክ/ከተማ ቀበሌ 12 ልዩ ቦታው አዲስ ከተማ ፖሊስ ፊት ለፊት በቀጠሮ ለመገናኘት ይስማማሉ፡፡

ከዚህ በላይ በተጠቀሰው ቦታ ላይ 2ኛ፣ 3ኛና ከ5ኛ ተከሳሾች ከሌሎች ለጊዜው ካልተያዙ ሁለት የመከላከያ ሰራዊት ልብስ ከለበሱ ግለሰቦችና ማንነቱ ካልታወቀ ሹፌር ጋር በመሆን የግል ተበዳይን ካለ ምንም የህግ አግባብ “ትፈልጋለህ” በማለት በካቴና አስረው የ3ኛ ተከሳሽ ንብረት በሆነ ኮብራ መኪና ውስጥ አስገድደው ካስገቡት በኋላ ቦሌ ክ/ከተማ ልዩ ቦታው ቦሌ መድሃኒለም ቤተክርስቲን ጀርባ በመውሰድ “ቼኩን አምጣ ወይም 400,000 /አራት መቶ ሺህ/ ብር ወስጃለሁ ብለህ ፈርም” በማለት በግል ተበዳይ ላይ ድብደባ መፈጸማቸውን የክስ መዝገቡ ይዘረዝራል፡፡

የግል ተበዳይም የተባለውን ለመፈጸም ፈቃደኛ ሳይሆን ሲቀር ተከሳሾቹ በካቴና አስረው ወደ ቂርቆስ ክ/ከተማ ላንቻ ፓሊስ ጣቢያ የወሰዱት ሲሆን 1ኛ ተከሳሽ ም/ኮማንደር ግርማ ሰንበቶ ህግን የማስከበር ግዴታ እያለበት የተሰጠውን ስልጣን በግልጽ ተግባር አላግባብ በመገልገል የግል ተበዳይ ታስሮ እንዲያድር ለተረኛ ፖሊሶች ትዕዛዝ በመስጠቱ የግል ተበዳይ ከሕግ አግባብ ውጪ በካቴና ወንበር ላይ ታስሮ ፓሊስ ጣቢያ እንዲያድር አድርገዋል፡፡ በመሆኑም ሁሉም ተከሳሾች በመላው ሃሳባቸውና አድራጎታቸው በወንጀሉ ድርጊትና በሚሰጠው ውጤት ሙሉ ተካፋይ በመሆን በግል ተበዳይ መብት ላይ ጉዳት በማድረሳቸው ተከሳሾቹ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በፈፀሙት በስልጣን ያለአግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ እንደተመሰረተባቸው ለመረዳት ተችሏል፡፡

በሌላ በኩል በ2ኛ፣ 3ኛ፣ 5ኛ ተከሳሾች ላይ የተመሰረተው 2ኛ ክስ እንደሚያስረዳው በ1ኛ ክስ ላይ በተጠቀሰው ቀን ተከሳሾቹ በሙሉ ሀሳባቸውና አድራጎታቸው የወንጀሉ ተካፋይ በመሆን የግል ተበዳይ ሆነውን ግለሰብ በሀይል አፍነው በመውሰድ ያለአግባብ ነፃነቱን በማሳጣት በመብቱ ላይ ከፍተኛ በደል በማድረሳቸው በዋና ወንጀል አድራጊነት በፈፀሙት ሰውን የመጥለፍ ወንጀል መከሰሳቸው ታውቋል፡፡

ኮሚሽኑ በ2ኛና በ3ኛ ተከሳሾች ላይ የተመሰረተው 3ኛ ክስ እንደሚያስረዳው ግለሰቦቹ በ1ኛ ክስ እንደተጠቀሰው በሙሉ ሀሳባቸውና አድራጎታቸው ወንጀሉ ተካፋይ በመሆን በዋና ወንጀል አድራጊነት በግል ተበዳይ ላይ ታስቦ በሚፈፀም ከባድ የአካል ጉዳት የማድረስ ወንጀል መከሰሳቸው ታውቋል፡፡

በመሆኑም ተከሳሾቹ በኮሚሽኑ የቀረበባቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃ መከላከል ባለመቻላቸው ፍርድ ቤቱ ጥር 16 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት 1ኛ ተከሳሽ ም/ኮማንደር ግርማ ሰንበቶ በ2 ዓመት ከ3 ወር ጽኑ እስራትና በብር 1500 ፣ 2ኛ ተከሳሽ ፍቃዱ ኦልጅራ በ3 ዓመት ጽኑ እስራትና በብር 1000፣ 3ኛ ተከሳሽ አብዱራዛቅ ዑመር በ5 ዓመት ጽኑ እስራትና በብር 5500 ፣ 5ኛ ተከሳሽ ዓለም ገብሬ በ1 ዓመት ከ6 ወር ጽኑ እስራትና በብር 500  እንዲቀጡ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

   

 

በከባድ የእምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል የተከሰሰ ግለሰብ ተፈረደበት  

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ተገቢ ያልሆነ ብልፅግና ለማግኘት ከባድ የዕምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል ፈጽሟል በማለት ክስ በመሰረተበት ሰለሞን አርጋው ላይ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ጥር 15 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ግለሰቡ በ6 ዓመት ፅኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

የኮሚሽኑ ዐቃቤ ሕግ በግለሰቡ ላይ የመሰረተው ክስ እንደሚያስረዳው ግለሰቡ በአዲስ አበባ አስተዳደር የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች አገልግሎት የንብረት ግምጃ ቤት ሆኖ በሚሰራበት ወቅት መስሪያ ቤቱ ከሳቦላ ኢንተርናሽናል ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር የተለያዩ ዕቃዎች እንዲቀርቡለት የገባውን ውል ተከትሎ ነው፡፡

በዚህም መሰረት ግለሰቡ ሣቦላ የተባለው የግል ማህበር በውሉ መሰረት ያቀረበውንና የካቲት 19 ቀን 2001 ዓ.ም በተጻፈ የገቢ ደረሰኝ ላይ የተዘረዘሩትን የተለያዩ ንብረቶች ተረክቦ ገቢ ካደረገ በኃላ የንብረት ቆጠራ ሲደረግ ከተዘረዘሩት ንብረቶች ውስጥ ግምቱ ብር 177,036.70 (አንድ መቶ ሰባ ሰባት ሺህ ሰላሳ ስድስት ብር ከሰባ ሳንቲም) የሆነ ፈጣን የስምሪት ድንኳን አጉድሎ በመገኘቱ ከባድ የዕምነት ማጉዳል የሙስና ወንጀል ፈጽሟል፡፡

በመሆኑም ተከሳሹ ሰለሞን አርጋው በክስ ሂደቱ ኮሚሽኑ የቀረበበትን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች መከላከል ባለመቻሉ ከላይ በተጠቀሰው ቀን በ6 ዓመት ጽኑ እስራትና በ

ብር 5ሺህ እንዲቀጣ ፍርድ ቤቱ የቅጣት ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

   

 

በሥልጣን ያለአግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል የተከሰሱ 5 ግለሰቦች ተፈረደባቸው

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሥልጣን ያለአግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ በመሰረተባቸው አምስት የሥራ ኃላፊዎች ላይ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ታህሳስ 26 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት እስከ አራት ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

ውሳኔ የተላለፈባቸው አምስቱም ተከሳሾች ትራንስፖርት እና ኮንስትራክሽን ዲዛይን አክሲዮን ማህበር የሥራ ኃላፊዎች የነበሩ ናቸው፡፡ በዚህም መሠረት 1ኛ ተከሳሽ ልዑለቃል ካሴ የአክሲዮን ማህበሩ ሥራ አስኪያጅ፣ 2ኛ ተከሳሽ ሰለሞን ዮሐንስ የምህንድስና መምሪያ ኃላፊ፣ 3ኛ ተከሳሽ አስፋው ብርሃኔ የአስተዳደርና ፋይናንስ መምሪያ ኃላፊ፣ 4ኛ ተከሳሽ በላይነህ ደሳለኝ የህግ አገልግሎት መምሪያ ኃላፊ፣ 5ኛ ተከሳሽ በሃይሉ ዛፍ ወርቅ አገኝ የኦዲት መምሪያ ኃላፊ እንደነበሩ የኮሚሽኑ የክስ መዝገብ ያስረዳል፡፡

አክስዮን ማሕበሩ ጨረታ አውጥቶ ግዥ የፈጸመበትን ሪግ ተከትሎ 1ኛ ተከሳሽ ዕቃው በዉሉና በስፔስፊኬሽኑ መሰረት በትክክል እንዳልቀረበና ወደማህበሩ የዕቃ ግምጃ ቤት ገቢ እንዳልሆነ እንዲሁም ገቢ ከመሆኑም በፊት ሪፖርት ሳይቀርብለት ሳባ ኢንጂነሪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ለተባለው የዕቃው አስመጭ ድርጅት አሰራርን ባልተከተለ መንገድ የዕቃ ደረሰኝ (Acceptance Certificate) በመስጠትና መ/ቤቱ ላይ ጉዳት በማድረሱ ክስ የተመሰረተበት ነው፡፡

ሁለተኛ ተከሳሽ ሰለሞን ዮሐንስ በበኩሉ የኢንስፔክሽን ኮሚቴ ባቀረበው ሪፖርት ላይ የሪጉ አካል የሆነው የውሃ ፓምፕ በተቀመጠለት ስፔስፊኬሽንና certificate of origin መሰረት እንዳልተገዛ እንዲሁም አሮጌ መሆኑ ተገልጾለት እያለ አዲስ መሆኑ ተረጋግጣል በማለት ርክክብ እንዲፈጸም ለቴክኒካል ምህንድስና ዋና ክፍል በጽሑፍ ትዕዛዝ ከመስጠቱም በተጨማሪ ሚያዝያ 6 ቀን 1998 ዓ.ም ከሳባ ኢንጂነሪንግ ጋር በተደረገ ውይይት ተገዛ የተባለው የሪጉ የዉሃ ፓምፕ አሮጌና የማያገለግል መሆኑ ተገልጾለት እያለ ጉዳዩን ሆን ብሎ ወደ ጎን በመተው ክስ እንደተመሰረተበት ለመረዳት ተችሏል፡፡

ሶስተኛ ተከሳሽ አስፋው ብርሃኔም የተገዛው ሪግ ጉድለት እንዳለበት በኢንስፔክሽን ኮሚቴ የተረጋገጠ መሆኑን እያወቀ ዕቃው ከነጉድለቱ ገቢ እንዲደረግ ለግዥና ንብረት አስተዳደር ዋና ክፍል ትዕዛዝ በመስጠት፣ ለሳባ ኢንጂነሪንግ የመልካም ሥራ አፈጻጸም ዋስትና (Performace Bond) እንዲሰጥ በማድረግ፣ ከሳባ ኢንጂነሪንግ ጋር በተደረገው ውይይት ላይ ስለ ውሃ ፓምፕ የተገለጸውን ጉዳይ ወደ ጎን በመተው ተገቢ ያልሆነ ስምምነት በመፈጸሙና የዕቃ ደረሰኝ (Acceptance Certificate) እንዲጻፍ አድርጎ መፈረሙ በክስ መዝገቡ ተገልጿል፡፡

አራተኛ ተከሳሽ በላይነህ ደሳለኝ በተጠቀሰው የውይይት መድረክ ላይ መ/ቤቱን ወክሎ በአባልነት በተወያየበት ወቅት በሙያ ተግባሩ የመስሪያ ቤቱን ጥቅም የማስከበርና ህጋዊ ተግባራትን ማከናወን ሲገባው የተገዛው ሪግ የውሃ ፓምፑ አሮጌና የማያገለግል መሆኑ ተጠቅሶለት እያለ የመ/ቤቱን ጥቅም በሚጎዳ አኳኋን ስለውሃው ፓምፕ የተገለጸዉን ወደ ጎን በመተው የዕቃ ደረሰኝ (Acceptance Certificate) ላይ በመፈረም ፣5ኛ ተከሳሽ በሃይሉ ዛፍ ወርቅ አገኝ ደግሞ በውይይቱ ላይ ቃለ-ጉባኤ ያዥና አባል ሆኖ በሚሰራበት ጊዜ የውኃ ፓምፑ አሮጌ እና የማያገልግል ስለመሆኑ በቃለ-ጉባኤው ውስጥ ሳያካትት በማለፉ የመ/ቤቱ ጥቅም እንዲጎዳ በማድረጉና የዕቃ ደረሰኝ (Acceptance Certificate) ላይ በመፈረሙ ክስ እንደተመሰረተባቸው ከክስ መዝገቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በአጠቃላይ ሁሉም ተከሳሾች ኮሚሽኑ በክስ ሂደቱ ያቀረበባቸውን የሰውና የሰነድ መስረጃዎች መከላከል ባለመቻላቸውና በፈጸሙት በሥልጣንን ያለአግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል  ውስጥ በሙሉ ፈቃዳቸውና እውቀታቸው ሙሉ ተካፋዮችና ግብርአበሮች መሆናቸው በፍርድ ቤቱ ስለተረጋገጠ 1ኛ እና 2ኛ ተከሳሾች እያንዳንዳቸው በ3 ዓመት ከ6 ወር ጽኑ እስራትና በ2 ሺህ ብር፤ 3ኛ፣4ኛ እና 5ኛ ተከሳሾች እያንዳንዳቸው በ4 ዓመት ጽኑ እስራትና በ2 ሺህ ብር እንዲቀጡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

   

 

በሀሰተኛ ሰነድ መገልገል የሙስና ወንጀል የተከሰሱ ሁለት ግለሰቦች ተፈረደባቸው

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሀሰተኛ ሰነድ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ በመሰረተባቸወ ሁለት ግለሰቦች ላይ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ታህሳስ 25 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት እስከ 5 ዓመት ተኩል በሚደርስ ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

የኮሚሽኑ ዐቃቤ ህግ በግለሰቦቹ ላይ የመሰረተው ክስ እንደሚያስረዳው 1ኛ ተከሳሽ ግርማ ሞገስ በቦሌ ክፍለ ከተማ የመሬት ግንባታ ፈቃድ ጽ/ቤት የከባቢያዊ የመረጃ መረብ (Geographical Information System /GIS/ ) ባለሙያ፣ 2ኛ ተከሳሽ ነጋልኝ ወልደሚካኤል በግል ሥራ የሚተዳደር ሲሆኑ 1ኛ ተከሳሽ 2ኛ ተከሳሽን ለመጥቀምና ለራሱም ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለማግኘት በማሰብ ከ1995-1997 ዓ.ም በነበረው ጊዜ ውስጥ ለ2ኛ ተከሳሽ የመኖሪያ ቤት  መስሪያ ቦታ በሊዝ ዕጣ የደረሰውና የሊዝ ውል የተዋዋለ በማስመሰል ሀሰተኛ የሊዝ ውል እና የይዞታ መረጋገጫ ካርታ ማዘጋጀቱን የክሱ ዝርዝር ያስረዳል፡፡

በተጨማሪም ከአዲስ አበባ የመሬት ልማትና አስተዳደር ባለስልጣን ለቦሌ ክፍለ ከተማ መሬት አስተዳደር ጽ/ቤት የተጻፈ በማስመሰል ካርታው ለ2ኛ ተከሳሽ የተሰጠ መሆኑን የሚገልጽ ሀሰተኛ ደብዳቤ በማዘጋጀት ህገ ወጥ ድርጊት መፈጸሙ በክስ መዝገቡ ላይ ተመልክቷል፡፡

2ኛ ተከሳሽ ነጋልኝ ወልደሚካኤል በበኩሉ 1ኛ ተከሳሽ ግርማ ሞገስ ያዘጋጀለትን ሀሰተኛ ሰነዶች በመጠቀም በክፍለ ከተማው ቀበሌ 15 ክልል ውስጥ የሚገኝ የሊዝ ዋጋ ግምቱ 826,000 (ስምንት መቶ ሃያ ስድስት ሺህ) የሆነ 175 ካ.ሜ መሬት በመውሰድና ጅምር የቤት ግንባታ በመሸጡ ክስ እንደተመሰረተበት የክስ መዝገቡ ያስረዳል፡፡

በአጠቃላይ ሁለቱም ተከሰሾች ሀሰተኛ ማህተሞችንና ፊርማዎችን በመጠቀም ያዘጋጇቸውን ሀሰተኛ ሰነዶች የያዘና በ2ኛ ተከሳሽ ስም የተዘጋጀ ሀሰተኛ ማህደር በህገ ወጥ መንገድ በቦሌ ክፍለ ከተማ መዝገብ ቤት እንዲገባ በማድረግና በቦታው ላይ ጅምር የመኖሪያ ቤት በመሸጥ ለግል ጥቅማቸው ያዋሉ በመሆኑ በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን በፈጸሙት ሀሰተኛ ሰነድ የማዘጋጀትና የመገልገል የሙስና ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡

ተከሳሾቹም በክሱ ሂደት የቀረበባቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን መከላከል ባለመቻላቸው 1ኛ ተከሳሽ ግርማ ሞገስ በ3 ዓመት ከ6 ወር፣ 2ኛ ተከሳሽ ነጋልኝ ወልደሚካኤል በ5 ዓመት ከ6 ወር ጽኑ እስራት እንዲቀጡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ታህሳስ 25 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ወስኗል፡፡

   

 

ወደ 6 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ የመንግስት ገንዘብ በመመዝበር የተጠረጠሩ በቁጥጥር ስር ዋሉ

በአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በዱብቲ ወረዳ የሚገኘው የተንዳሆ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት የሥራ ኃላፊዎችን፣ የወረዳው የፋይናንስና የኢኮኖሚ ልማት ኃላፊንና ሌሎች ሰራተኞችን እንዲሁም ሁለት የዱብቲ ከተማ ነዋሪዎችን ጨምሮ 10 ግለሰቦች ወደ 6 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ የመንግስት ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በሚል ተጠርጥረው በፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡

ኮሚሽኑ ተጠርጣሪዎቹን በቁጥጥር ስር ያዋላቸው ግለሰቦቹ የተንዳሆ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት የተለያየ አገልግሎት ከሚሰጡት ድርጅቶች የሰበሰበውን ዊዝሆልዲንግ ታክስ (withholding tax) ለዱብቲ ወረዳ ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ጽ/ቤት የገባ በማስመሰል ለግል ጥቅማቸው አውለዋል በሚል ነው፡፡

ተጠርጣሪዎቹ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዱብቲ ቅርንጫፍ በተንዳሆ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ስም ከተከፈተው የባንክ ሂሳብ ላይ ከላይ የተጠቀሰው የገንዘብ መጠን በተለያዩ ጊዜያት በግለሰቦች ስም በቼክ ወጪ ሆኖ እንዲከፈል በማድረግ እና ገንዘቡን ከባንክ በማውጣት ወንጀሉን በግብረ-አበርነት ፈጽመዋል በሚል ተጠርጥረው ተጠያቂ ሆነዋል፡፡

ግለሰቦቹ በተለያዩ ቀናት በቁጥጥር ስር ከዋሉ በኋላ ታህሳስ 24 ቀን 2004 ዓ.ም ፍርድ ቤት ቀርበው የ14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ተጠይቆባቸው ምርመራ እየተጣራባቸው እንደሚገኝም ታውቋል፡፡

   

 

የኮሚሽኑ ሠራተኞች የዘንድሮውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ከበሩ

በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ8ኛ ጊዜ በአገራችን ደግሞ ለ7ኛ ጊዜ ዘንድሮ የተከበረውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሠራተኞች ታህሳስ 20 ቀን 2003 ዓ.ም በኮሚሽኑ የስብሰባ አዳራሽ በዓሉን በፓናል ውይይት እና በልዩ ልዩ ዝግጅቶች አከበሩ፡፡ በዝግጅቱ መክፈቻ ላይ የኮሚሽኑ ም/ኮሚሽነር ክቡር አቶ አዲሱ መንግስቱ በተወካያቸው አማካኝነት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ክቡር ም/ኮሚሽነሩ ባስተላለፉት መልዕክት ሙስና በዓለማችን ላይ ከፍተኛ አደጋ ከደቀኑት ችግሮች መካከል አንዱና ዋነኛው እንደሆነ ጠቅሰው፣ የዓለም ህዝብ ይህን ማኅበራዊ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጠንቅ በአግባቡ መከላከል እና መዋጋት ካልቻለ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን እንዲሁም ሰላምና መረጋጋትን ማስፈን እንደማይቻል ገልጸዋል፡፡  ሙስና  በባህሪው ድንበር ዘለል በመሆኑ ሁሉም አገሮች ተባብረው ሊመክቱት እና ሊያሸንፉት የሚገባ  ጉዳይ መሆኑንም ጨምረው አስገንዝበዋል፡፡

ለተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አባል አገራት እ.ኤ.አ ከዲሴምበር 9-12 ቀን 2003 ለፊርማ የቀረበውና በበርካታ አገሮች የፀደቀው የተባበሩት መንግሥታት የፀረ-ሙስና ኮንቬንሽን እውን መሆን በዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ትግል ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ የሚሰጠው ክንዋኔ መሆኑንም ክቡር ም/ኮሚሽነሩ ገልጸው፣ ኮንቬንሽኑ ለአባል አገራት ለፊርማ የቀረበበት የመጀመሪያ ቀን በየዓመቱ ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን ሆኖ  እንዲከበር በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በተወሰነው መሠረት በዓሉ በተለያዩ አገሮች ዘንድ በተለያዩ ዝግጅቶች ሲከበር መቆየቱን አስረድተዋል፡፡

ክቡር ም/ኮሚሽነሩ አክለውም የዚህ ኮንቬንሽን ፈራሚና አጽዳቂ የሆነችው አገራችንም በዓሉን በየዓመቱ በማክበር በፀረ-ሙስና ትግሉ ያላትን ተሳትፎ እና ቁርጠኝነት ስታሳይ መቆየትዋን አስታውሰው፣ የዘንድሮውን በዓልም አገሮች «Act Against Corruption Today!»  በሚል መሪ-ቃል እያከበሩት እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡

ዕለቱ  በተዘጋጀው  የፓናል ውይይት ላይ ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ. የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና ከውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የተጋበዙ  ባለሙያዎች በአባይ ወንዝ ተፋሰስ እና በታለቁ የህዳሴ ግድብ እንዲሁም በአጠቃላይ በውሃ ሀብታችን ዙሪያ ጥናታዊ ጽሑፍ ያቀረቡ ሲሆን ይህን ተከትሎም በኮሚሽኑ ሠራተኞች በተነሱ ጥያቄዎች ላይ የተሰጡት ማብራሪያዎች ለተሳታፊዎች ተጨማሪ ግንዛቤ የፈጠሩ እንደነበሩ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ከዚህ ጋር በተያያዘ ከኢትዮጵያ ሴት ደራሲያን ማህበር በተጋበዙ የኪነጥበብ ባለሙያዎች የቀረቡትና የሙስናን አስከፊነት የሚያሳዩ ልዩ ልዩ ግጥሞችና መነባንቦች ለዝግጅቱ ልዩ ድምቀት  የሰጡ .መሆናቸውን ለመረዳት ተችሏል

የአምስት ዓመቱን የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ተግባራዊ በማድረግ ድሕነትን ለማስወገድ በሚደረገው ጥረት ኪራይ ሰብሳቢነትና የእርሱ መገለጫ የሆነው ሙስና እንቅፋት እንዳይሆኑ ከመታገልና በዚህ ዓላማ ዙሪያ ከማስተባበር አንጻር በአገራችን ደረጃ ለዘንድሮው ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን #ሙስናን መዋጋት ድህነትን መዋጋት ነው!; የሚለው መሪ-ቃል  እንደተመረጠ ለማወቅ ተችሏል፡፡

   

 

ኮሚሽኑ በህገ-ወጥ መንገድ ስልክ ሲያስደውሉ በነበሩ ተጠርጣሪዎች ላይ የቅድመ ክስ መግለጫ ማሰማት ጀመረ

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሕገ-ወጥ መንገድ ስልክ ወደ ውጭ አገር ሲያስደውሉ በነበሩ 24 ግለሰቦችና በወንጀሉ ተባባሪ በነበሩ 42 የቀድሞ የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን ሰራተኞች ላይ የመሰረተውን ክስ በማስመልት ከታህሳስ 18 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮ በፌደራል ከፍተኛ  ፍርድ ቤት የቅድመ ክስ መግለጫ ማሰማት ጀመረ፡፡

ኮሚሽኑ በተጠርጣሪዎቹ ላይ የመሠረተው ክስ እንደሚያስረዳው ግለሰቦቹ ምንም ዓይነት ሕጋዊ ድርጅትና ከመንግስት አካል የተሰጣቸው ሕጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው በማይታወቅ ድርጅት ስም ከኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን የቀጥታ ስልክ መስመር አገልግሎት ለማግኘት ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡

በወቅቱ ሥራ ላይ የነበሩ የኮርፖሬሽኑ የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች በበኩላቸው እነዚህ ግለሰቦች በማይታወቅ ድርጅት ስም ያቀረቧቸውን የቀጥታ ስልክ መስመር አገልግሎት ጥያቄ ሕጋዊነቱን ሳያረጋግጡና ይልቁንም የወንጀሉ ተባባሪ በመሆን በሕገወጥ መንገድ የአገልግሎት ፈቃድ እንዲያገኙ ማድረጋቸውም በክሱ ላይ ተመልክቷል፡፡

ተጠርጣሪዎቹም ከኮርፖሬሽኑ ፈቃድ ካገኙ በኋላ እስከ አንድ መቶ የሚደርሱ ቀጥታ የስልክ መስመሮችን በአንድ ወይም በሁለት ክፍል ቤት ውስጥ በማስገባት፣ የተለያዩ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን በመጠቀምና ከሳተላይት ዲሽ ጋር በማገናኘት ወደ ውጭ አገር ስልክ በማስደወላቸው ምክንያት መንግስት ሊያገኝ ይገባው የነበረ የ289 ሚሊዮን ብር ያህል ገቢ ማሳጣታቸው ታውቋል፡፡

በዚሁ መሠረት ኮሚሽኑ በ66ቱ ተጠርጣሪ ግለሰቦች ላይ መረጃዎችን በማሰባሰብና በአምስት የክስ መዝገቦች በማደራጀት ከታህሳስ 18 እስከ ጥር 7 ቀን 2004 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመቅረብ በተከሳሾቹ ላይ የቅድመ ክስ መግለጫ እንደሚያሰማ ታውቋል፡፡

   

 

ኮሚሽኑ ከUNDP ጋር በመተባበር ያሳተመው ቢል ቦርድ ተመረቀ

ዘንድሮ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ8ኛ ጊዜ ዲሴምበር 9 የተከበረውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን በማስመልከት በፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እና በተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) የጋራ ትብብር በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለገሐር አካባቢ የተሰራው ቢል ቦርድ የኮሚሽኑ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም ተወካዮች በተገኙበት ታህሳስ 12 ቀን 2004 ዓ.ም ተመረቆ ለሕዝብ እይታ ክፍት ሆነ፡፡

በምረቃ ሥነሥርዓቱ ላይ የኮሚሽኑ ም/ኮሚሽነር ክቡር አቶ አዲሱ መንግስቱ ባደረጉት ንግግር የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም ለዴሞክራቲክ ተቋማት የሚያደርገው ድጋፍ ኮሚሽኑ በፀረ-ሙስና ትግሉ ዙሪያ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የበለጠ እንዲጎለብት አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸው፣ ፕሮግራሙ የኮሚሽኑን የመፈጸም አቅም በማጎልበት፣ ሥነምግባርን በማስፋፋትና የፀረ-ሙስና ትግሉን በማቀጣጠል ዙሪያ የህብረተሰቡን ዕውቀትና ግንዛቤ በማሳደግ፣ ሙስናን በመከላከል እንዲሁም በዘርፉ የሚከሰቱ የህግ ጥሰቶችን መርምሮ ለፍርድ በማቅረብ ረገድ ትልቅ ዕገዛ እያደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

አንደ ም/ኮሚሽነሩ ገለጻ በአለም አቀፍ ደረጃ ለ8ኛ ጊዜ የሚከበረውን የአለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀንን በተመለከተ በእንግሊዘኛው ቋንቋ «Act Against Corruption Today!» በሚል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአደንዛዥ ዕፆች እና የወንጀል ቢሮ (United Nations Office on Drugs and Crime, UNODC) ያወጣውን መሪ-ቃል መሰረት በማድረግ ኮሚሽኑም «የፀረ-ሙስና ትግሉን አሁኑኑ ይቀላቀሉ!» የሚለውን አቻ ትርጉም በመጠቀም ቢል ቦርዱ እንዲተከል ማድረጉን አስገንዝበዋል፡፡

ለምረቃ በበቃው ቢል ቦርድ ላይ የወጣው መልዕክት በአንድ በኩል በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸደቀው ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ኮንቬንሽን ተግባራዊ እየሆነ እንደሚገኝ የሚያመለክት ሲሆን፣ በሌላ በኩል UNDP በአገራችን እየተካሄደ ለሚገኘው የፀረ-ሙስና ትግል ለሚያደርጋቸው እገዛዎች እንደ አንድ ማሳያ ተደርጎ የሚወሰድ ነው፡፡

ኮሚሽኑ ዘንድሮ በአገራችን ለ7ኛ ጊዜ የሚከበረውን የዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀንን «ሙስናን መዋጋት ድህነትን መዋጋት ነው!» በሚል መሪ ቃል እያከበረ በሚገኝበት ወቅት የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) ከኮሚሽኑ ጋር በመተባበር የዘንድሮውን የዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀንን በሚመለከት በዓለም አቀፍ ደረጃ የተዘጋጀውን መልዕክት የያዘ ቢል ቦርድ ታትሞ እንዲተከል ማድረጉ በሕብረተሰባችን ዘንድ ተጨማሪ ግንዛቤ ለመፍጠር ትልቅ አስተዋፅኦ እንደሚያደርግ ም/ኮሚሽነሩ አክለው ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) ዳይሬክተርና ተወካይ የሆኑት ሚስስ አሌሳንደራ ቲሶት በበኩላቸው በምረቃው ላይ ተገኝተው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሴክሬተሪ ጄነራልን መልዕክት ባስተላለፉበት ወቅት እንደገለጹት ሙስና ሁሉንም የዓለማችንን አገራት የሚጎዳ፣ ማህበራዊ ለውጦችን የሚገታ፣ በተለይም በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎች በትምህርት፣ በጤና እና በማህበራዊ አገልግሎቶች ዘርፍ ተጠቃሚ እንዳይሆኑ በማድረግ እኩልነትንና ፍትህን የሚያዛባ በመሆኑ ሁሉም ዜጋ ሊዋጋው እንደሚገባ ከማሳሰባቸውም በተጨማሪ የዘንድሮውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀንን ስናከብር ሙስናን በማጋለጥ፣ ሙሰኞች በድርጊታቸው እንዲያፍሩ በማድረግና የመልካም ሥነምግባር ባህልን በማጎልበት በፀረ-ሙስና ትግሉ ዙሪያ የበኩላችንን ልንወጣ ይገባል ብለዋል፡፡

የዘንድሮውን የዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን በማስመልከት በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) በዴሞክራቲክ ተቋማት ፕሮግራም (DIP) በኩል ከሚያደርገው ድጋፍ በተጨማሪ በዘንድሮው በጀት ዓመት  2 ቢል ቦርዶች፣ 1 ባነር፣ 9 ዓይነት ፖስተሮች፣ 1 ሊፍሌት በተለያየ መጠን ታትመው ለህብረተሰቡ እንዲደርሱ መደረጉን ለማወቅ ተችሏል፡፡

   
 

ሚሽኑ 50 ለሚሆኑ አዳዲስ የሥነምግባር መኮንኖች ሥልጠና ሰጠ

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከተለያዩ መስሪያ ቤቶች ለተዉጣጡ 50 ለሚሆኑ አዳዲስ የሥነምግባር መኮንኖች ከታህሳስ 10 – 13 ቀን 2004 ዓ.ም በዋቢ ሸበሌ ሆቴል የስብሰባ አዳራሽ ስልጠና ሰጠ፡፡

ስልጠናዉ የሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች ዓመታዊ ዕቅድና ሪፖርት አዘጋጃጀት፣ ክፍሎቹን አስመልክቶ ስለወጣ ደንብ እንዲሁም በሌሎች እንቅስቃሴዎች ላይ ያተኮረ ሲሆን በተጨማሪም ሰልጣኞቹ በሚሰሩባቸው መስሪያ ቤቶች ለሚገኙ ሰራተኞች በሥነምግባር እና በፀረ-ሙስና ላይ ያተኮሩ ትምህርቶችን ለማሰራጨት በሚያስችላቸው ሁኔታ ላይ ማብራሪያ የተሰጠ መሆኑን ለመረዳት ተችሏል፡፡

ለሰልጣኞቹ በሥራ ዲሲፒሊን፣ በሙያ ሥነምግባር እና በህዝብ አገልጋይነት ላይ ገለጻ የተደረገላቸው ሲሆን ሥልጠናው በሚሰሩበት መስሪያ ቤት የሚገኙ ሰራተኞችን በፀረ- ሙስና ትግሉ የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ብልሹ አሰራርን እና የሙስና ወንጀልን በማጋለጥ እንዲመረመርና በጥፋተኞች ላይ ተገቢው እርምጃ እንዲወሰድ በማድረግ ረገድ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት እንደሚያስችላቸው ታውቋል፡፡

ኮሚሽኑ በመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ በልማት ድርጅቶችና በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሙስናና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል የሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች እንዲቋቋሙ፣ እንዲደራጁና ስራቸውን በአግባቡ እንዲወጡ የሚያስችሉ በርካታ እንቅስቃሴዎችን በማከናወን ላይ የሚገኝ ሲሆን በዚህ ጥረቱ በፀረ-ሙስና ትግሉ ጉልህ ሚና ያላቸውን አካላትና የህብረተሰብ ክፍሎች የሚያስተባብሩ 244 የሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች እንዲደራጁ ማድረጉን ለመረዳት ተችሏል፡፡

   

 

የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች እንዲሁም አግባብነት ያላቸው አካላት 11ኛ የጋራ ጉባኤ ተካሔደ

የፌደራል እና የክልል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች እንዲሁም አግባብነት ያላቸው አካላት የጋራ ጉባኤ 11ኛ መደበኛ ስብሰባ ከታህሳስ 5-6 ቀን 2004 በጎንደር ከተማ ተካሄደ፡፡ ጉባኤው በአማራ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንት በአቶ አያሌው ጎበዜ ንግግር የተከፈተ ሲሆን  በተለያዩ አጀንዳዎች ላይም መክሯል፡፡ 

ለሁለት ቀናት በቆየው ጉባኤ በቀዳሚነት የ2003 በጀት ዓመት ሀገር አቀፍ የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ ሪፖርት ቀርቦ ሰፊ ውይይት የተደረገበት ሲሆን በሪፖርቱ ላይ በተሳታፊዎቹ የተሰነዘሩ አስተያየቶች ከተካተቱ በኋላ እንደሚጸድቅ ይጠበቃል፡፡

ጉባኤው በተጨማሪም የሀገር አቀፍ የፀረ-ሙስና ጥምረት የአራት ዓመታት (2004-2007) ስትራቴጂክ ዕቅድ ረቂቅ ላይ ተወያይቶ ይህን ሀገር አቀፍ ሰነድ ለማዳበር የሚረዱ ሀሳቦች ቀርበውና ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸው ረቂቅ ዕቅዱ ጸድቋል፡፡

የፌዴራል እና የክልል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች የኢትዮጵያን የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ (GTP) ለማሳካት እያደረጉ ያለውን እንቅስቃሴ እንዲሁም የፌዴራል መንግስት ለክልል መንግስታት ከሚሰጠው የበጀት ድጋፍ ጋር በተያያዘ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያለውን ተግባርና ኃላፊነት በተመለከተ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

የኢትዮጵያን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ (GTP) ለማሳካት የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች እያደረጉት ያለውን እንቅስቃሴ ለመገምገም ይረዳ ዘንድ የፌደራል እና የክልል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች ከዚህ አንጻር ያቀዷቸውንና ያከናወኗቸውን ተግባራትም ለተሰብሳቢዎች አስደምጠዋል፡፡

በቀረቡት ዕቅዶችና ክንውኖች ላይ በተደረገው ውይይት የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅዱን ለማሳካት የፀረ-ሙስና ትግሉ የሚጠበቅበትን ትክክለኛ ድርሻ ለይቶ ከመንቀሳቀስ አንጻር ጅምሮች እንዳሉና በቀጣይ ጊዜያትም የተሻለ እንደቅስቃሴ እንደሚጠበቅ ተጠቁሟል፡፡

በጉባኤው ማጠናቀቂያ ላይም የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን በ11ኛው የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖችና አግባብነት ያላቸው አካላት የጋራ ጉባኤ ላይ ከስምምነት የተደረሰባቸውን የውይይት ሀሳቦች ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት እንዲያደርጉ የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖችና አግባብነት ያላቸው አካላትን አሳስበዋል፡፡

ሀገራችን ከድህነት ተላቃ መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ጎን ያሰልፋታል ተብሎ የሚታሰበውን የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ተግባራዊ ለማድረግ ሙስናና ብልሹ አሰራርን እንዲሁም የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ ከስር መሰረቱ ማስወገድ ዋንኛ ተግባር እንደሚሆን ክቡር ኮሚሽነሩ ገልጸው፣ በዚህ ረገድ የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች የተረከቡት ኃላፊነት ከፍተኛ መሆኑን አስታውሰዋል፡፡

የክልል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች ዕቅዶቻቸው ከዚህ አንፃር የተቃኙ መሆናቸውን ለማረጋገጥ ክለሳ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸውም ጨምረው አስገንዝበዋል፡፡

በዚህ ረገድ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው የኮንትራት አስተዳደር፣ ትላልቅ የመንግስት ግዢና ሽያጭ፣ ግብርና ታክስ የመሳሰሉ ጉዳዮች የዕቅዶቹ ዋንኛ የትኩረት አቅጣጫዎች መሆን እንደሚኖርባቸውም አሳስበዋል፡፡

ከክቡር ኮሚሽነሩ ማብራሪያ ለመረዳት እንደተቻለው ከፌዴራል መንግስት ለክልል መንግስታት በሚሰጥ ድጎማ ላይ የሚፈጸም ሙስናና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል በጉዳዩ ላይ ወደፊት በቂ ትኩረት ተሰጥቶት የሚሰራ ሲሆን ለዚህ የሚያገለግል ፕሮሲጀር ተዘጋጅቶ ለውይይት ከቀረበ በኋላ በቂ የአቅም ግንባታ ስራ ተከናውኖ ተግባራዊነቱ ይጀመራል፡፡

በመጨረሻም ቀጣዩን የፌደራል እና የክልል ሥነምግባር እና ፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች እንዲሁም አግባብነት ያላቸው አካላት 12ኛ የጋራ ጉባኤን የአፋር ክልል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እንዲያዘጋጅ እድሉ ተሰጥቶታል፡፡  

የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖችና አግባብነት ያላቸው አካላት የጋራ ጉባኤ በየስድስት ወሩ የሚካሄድ ሲሆን ጉባኤው ሀገር አቀፍ የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴን በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ይመክራል፡፡ 

   

 

የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባላት ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀንን አከበሩ

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባላት ታህሳስ 5 ቀን 2004 ዓ.ም ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀንን በፓናል ውይይት አከበሩ፡፡

ምክር ቤቱ ያዘጋጀው ፓናል ውይይት የተካሄደው የኮሚሽኑ ዋነኛ የትኩረት መስኮች ከሆኑት መካከል በመሬት አስተዳዳር፣ በታክስ ስርዓትና በመንግስት ግዥ ዙሪያ የሚፈጸም ሙስናን በተመለከተ ሲሆን በዚህ መድረክ ላይ የኮሚሽኑ ባለሙያዎች በመገኘት ለምክር ቤቱ አባላት ገለጻ አድርገዋል፡፡

የመንግስት ግዥን በተመለከተ በኮሚሽኑ ባለሙያዎች በተሰጠው ማብራሪያ ላይ የግዥ አፈጻጸም መርሆዎች፣ የጨረታ ዝግጅት መርሆዎች እና የጨረታ ሰነድ ዝግጅት ሂደትን የተመለከተ ገለጻ ተደርጓል፡፡

በተመሳሳይም የሂሳብ ማጣሪያ በሚደረግብት ወቅት፣ ግዥ ተግባራዊ በሚሆንበት ሂደት እና በመንግስት ንብረት አወጋገድ ሂደት ሊከሰቱ ስለሚችሉ የሙስና ድርጊቶች፤ በግዥ ሒደት የሚፈጸም ሙስና ስለሚያስከትለው ጉዳት እንዲሁም በግዥ ሥርዓት ውስጥ የሚፈጸሙ ሙስናዎችን ለመከላከል ተግባራዊ ስለሚደረጉ ስልቶች ለምክር ቤቱ አባላት ገለጻ ተደርጎ በዚህ ዙሪያ ውይይት መካሄዱን ለመገንዘብ ተችሏል፡፡

ታክስ እና ግብር አገራዊ ገቢን ከማመንጨት አኳያ ከፍተኛ ድርሻ የሚይዝ እንደመሆኑ ከሙስና የጸዳ የታክስ እና ግብር ስርዓት ለሀገር ኢኮኖሚ ግንባታ ስለሚያበረክተው ወሳኝ ሚና በውይይቱ ላይ ተገልጿል፡፡

የምክር ቤቱ አባላት በተጨማሪም በግብር እና ታክስ አስተዳደር ሥርዓት ውስጥ ለሙስና ሊያጋልጡ ስለሚችሉ ግድፈቶች እና የሥነምግባር ችግሮች፣ በሠራተኞችና በተቋማት ስለተፈጸመ የሙስና ወንጀል ጠቋሚ ምልክቶች እንዲሁም ከዚህ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ የሙስና ወንጀሎች ስለሚያስከትሉት ጉዳት እና በችግሩ የመከላከያ ዘዴዎች ዙሪያ ውይይት አካሂደዋል፡፡

በውይይቱ ወቅት መሬት ሙስና ከሚፈጸምባቸው የሀገር ሃብቶች አንዱ እንደመሆኑ ይህን ሐብት ከሙስና ለመጠበቅ የመሬት አስተዳደር ሥርዓት በአግባቡ ተግባራዊ መሆን እንዳለበት እና ለስኬታማነቱ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትን ጨምሮ ሁሉም የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ሊረባረቡ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡

   

 

በውጤት ተኮር ክትትል፣ ግምገማና አፈጻጸም መመሪያ ላይ ስልጠና ተሰጠ

የኮሚሽኑ የጥናትና ለውጥ ሥራ አመራር ዳይሬክቶሬት በውጤት ተኮር ክትትል፣ ግምገማና የአፈጻጸም መመሪያ ላይ ከሁሉም የኮሚሽኑ የሥራ ሒደቶች የተውጣጡ 217 ሠራተኞች በሰባት ዙር የተሳተፉበት የግማሽ ቀን ስልጠና ከህዳር 25 - ታህሳስ 2 ቀን 2004 ዓ.ም ድረስ ተሰጠ፡፡

ስልጠናው በኮሚሽኑ ራዕይ፣ ተልዕኮና እሴቶች፣ በኮሚሽኑ ስትራቴጅክ እይታዎች፣ በስትራቴጅክ ግቦች፣ መለኪያዎችና ኢላማዎች፣ በውጤት ተኮር ድጋፍ፣ ክትትልና ግምገማ እንዲሁም በግለሰብ ፈፃሚዎች፣ በቡድን አስተባባሪዎች እና በሥራ ሒደት ኃላፊዎች የውጤት ተኮር አፈጻጸም ምዘና ላይ ያተኮረ ነበር፡፡

ስልጠናውን ከዚህ በላይ በተጠቀሱት ርዕሰ-ጉዳዮች ላይ ማዘጋጀት ያስፈለገው የኮሚሽኑ ሠራተኞች በኮሚሽኑ ስትራቴጅክ ዕቅድ ላይ ያላቸውን ግንዛቤ አስመልክቶ በተካሄደው ጥናት የተገኘው ውጤት አበረታች ሆኖ ባለመገኘቱ ምክንያት ስትራቴጅክ ዕቅዱን ለማስረጽ እንዲሁም በውጤት ተኮር አፈጻጸም ላይ በቂ ግንዛቤ ይዘው ውጤታማ ሥራ ለማከናወን እንዲችሉ መሆኑን ከዳይሬክቶሬቱ የተገኘው መረጃ አመልክቷል፡፡

በሥልጠናው ላይ እያንዳንዱ ግለሰብ ፈጻሚ ሳምንታዊ ዕቅድ እያዘጋጀ ሥራውን በማከናወንና መረጃ በመያዝ ሳምንታዊ ሪፖርት ማዘጋጀት እንደሚገባው፣ እንዲሁም በየወሩ መጨረሻ የዕቅድ ክንውን ሪፖርት በማዘጋጀት ከቡድን አስተባባሪው ጋር መፈራረም እንደሚኖርበት ተገልጿል፡፡

ውጤት አሰጣጥን በተመለከተ በቀረበው ማብራሪያ የግለሰብ ፈጻሚዎች አማካይ ውጤት የቡድን አስተባባሪ ውጤት እንደሚሆን፣ የቡድን አስተባባሪዎች አማካይ ውጤት ደግሞ የሥራ ሒደት መሪ ውጤት ሆኖ እንደሚሰጥ ለመገንዘብ ተችሏል፡፡

የቡድን አስተባባሪዎች የግለሰብ ፈጻሚዎችን የግማሽ ዓመት አማካይ ውጤት ወደ ስትራቴጅያዊ ግቦች በመመንዘር እና በዕቅዱ ከተቀመጡት መለኪያዎች አንጻር ዒላማዎች መሳካታቸውን የማረጋገጥ ሥራ የሚያከናውኑ መሆናቸው ታውቋል፡፡

በመሆኑም ስልጠናው እያንዳንዱ ግለሰብ ፈጻሚ ሥራውን ሲያከናውን በኮሚሽኑ ራዕይ፣ ተልዕኮ እና እሴቶች ላይ ግልጽ ግንዛቤ ይዞ የዕለት ተዕለት ሥራውን እንዲያከናውን የሚረዳ መሆኑንም የሥልጠናው አዘጋጆች ገልፀዋል፡፡

በሌላ በኩል የእያንዳንዱ ግለሰብ ፈፃሚ የውጤት ተኮር የአፈጻጸም ምዘና በየስድስት ወሩ የሚካሔድ ሲሆን፣ የመጀመሪያው ስድስት ወር አፈጻጸም ምዘና ከሐምሌ 1 - ታህሳስ 30 የሁለተኛው ስድስት ወር የአፈጻጸም ምዘና ደግሞ ከጥር 1 - ሰኔ 30 ያለውን ጊዜ የሚሸፍን ሆኖ የመጀመሪው የአፈጻጸም ምዘና ከታህሳስ 25-30 ፣ የሁለተኛው ደግሞ ከሰኔ 25-30 ባለው ጊዜ ውስጥ ተሞልቶ እንዲጠናቀቅም ለመረዳት ተችሏል፡፡

በመሆኑም የቡድን አስተባባሪዎች የግለሰብ ፈፃሚዎችን የማብቃትና ድጋፍ የማድረግ ሥራ በተከታታይ ተግባራዊ በማድረግ የውጤት መረጃዎችን በአግባቡ እንዲይዙ፣ የግለሰብ ፈጻሚዎችም በውጤት ተኮር ክትትል አፈጻጸም መመሪያ ላይ የተቀመጡትን ቅጾች በመጠቀም የዕለት-ተዕለት ተግባራቸውን በማከናወን ሪፖርት ማቅረብ እንደሚገባቸው ከሥራ ሂደቱ ተገልጿል፡፡

በሌላ በኩል ግለሰብ ፈፃሚዎች በጣም ከፍተኛ ውጤት ሲያመጡ ሊበረታቱ የሚችሉበትን የማበረታቻ ሥርዓት ለመዘርጋት ዝግጅት እየተካሄደ እንደሚገኝም ለመረዳት ተችሏል፡፡

   

 

የኮሚሽኑ ሰራተኞች የነጭ ሪቫን እና የዓለም ኤድስ ቀንን አከበሩ

የፌዴራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሠራተኞች የዓለም አቀፉን የነጭ ሪቫን እና የዓለም የኤድስ ቀን ህዳር 28 ቀን 2004 ዓ.ም በተለያዩ ዝግጅቶች አከበሩ፡፡

የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር ክቡር አቶ አዲሱ መንግስቱ ዝግጅቱን በንግግር ሲከፍቱ እንደገለጹት የነጭ ሪቫን ቀን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚከበርበት ምክንያት ጾታን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶች የሰብዓዊ መብት ጥሰት እና ልማትን የሚያደናቅፉ ድርጊቶች መሆናቸውን ሕብረተሰቡ ግንዛቤ እንዲጨብጥ በማስቻል መንግስታት የኃይል ጥቃትን ለማስወገድ የገቡትን ቃል እንዲፈጽሙ ግፊት ለማድረግ እንዲሁም በየአካባቢው የሚደረጉ የጸረ-ጾታዊ ጥቃት ትግሎችን ለማጠናከር እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

የነጭ ሪቫን ቀን በሀገራችን የሚከበረው በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ የተለያዩ ጥቃቶችን መዋጋት አስፈላጊ መሆኑን ለመጠቆም እንዲሁም የሴቶችን መብት አስመልክተው የወጡ ህጎችን እና በዓለም አቀፍ ደረጃ የተፈረሙ ስምምነቶች ተፈጻሚ እንዲሆኑ አጽንኦት ለመስጠት መሆኑን ምክትል ኮሚሽነሩ አብራርተዋል፡፡

የነጭ ሪቫን ቀን ሲከበር በሴቶች ላይ የሚደርሱ የተለያዩ ጥቃቶችን በጋራ ለመከላከል እና ለማስቆም የሚደረገውን ጥረት ለመግለጽ ወንዶች በደረታቸው ላይ ነጭ ሪቫን በማድረግ አጋርነታቸውን የሚገልጹ ሲሆን የበዓሉ ስያሜም ከዚሁ የመነጨ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

በሌላ በኩል በዓለም አቀፍ ደረጃ የዘንድሮው የዓለም ኤድስ ቀን “አንድም ሰው በኤች.አይ.ቪ እንዳይያዝ፣ እንዳይገለልና እንዳይሞት ኃላፊነታችንን እንወጣ” በሚል መሪ-ቃል በመከበር ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ በሀገራችን ደግሞ ከእናት ወደ ልጅ እና በአዋቂዎች መካከል ያለውን የቫይረሱን መተላለፍ ለማስቀረት የሚመለከታቸው ሁሉ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ እንዳለባቸው በሚያሳስብ መልኩ “አንድም ሰው በኤች.አይ.ቪ እንዳይያዝ ኃላፊነታችንን እንወጣ”  በሚል መሪ-ቃል ዙሪያ በመከበር ላይ እንደሚገኝ አቶ አዲሱ ጠቁመዋል፡፡

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ባለፉት ዓመታት በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን ለመከላከል እና ለማስቆም እንዲሁም የኤች.አይ.ቪ/ኤድስ የበሽታ ስርጭት እንዲቀንስ በማድረግ የበኩሉን ድርሻ ሲወጣ መቆየቱን ም/ኮሚሽነሩ ገልጸው፣ ኮሚሽኑ በሴቶች እና በፀረ ኤች አይ.ቪ ኤድስ ጉዳዮች ዙሪያ ተጠሪ በመሆን የሚሰሩ ባለሙያዎችን በመመደብ እና ይህን ዓላማ ለማስፈጸም እንዲረዳ የተለያዩ ወጪዎችን ለመሸፈን የሚያስችል በጀት በመመደብ የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን በማድረግ ላይ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

ኮሚሽኑ በሕገመንግስታችንና በሌሎችም የሀገራችን ሕጎች የተደነገጉትን የሴቶች መብት ከማስከበር አልፎ በኮሚሽኑ የሚገኙ የሴት ሠራተኞችን ቁጥር ለመጨመር እንዲቻል በ2004 በጀት ዓመት 50 ሴት ባለሙያዎችን ለመቅጠር በዝግጅት ላይ የሚገኝ መሆኑን ገልጸው፣ ሌሎች የመንግስት ተቋማትም ተመሳሳይ እንቅስቃሴ ቢያደርጉ ጠቃሚ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በኮሚሽኑ የሥርዓተ ጾታ ፎካል ፐርሰን የሆኑት ወ/ሮ ሰብለ ወንጌል ፍቃዱ በጾታ ጥቃት ዙሪያ ባቀረቡት ጽሁፍ እንደጠቆሙት ጾታን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶች በየትኛውም የህብረተሰብ ክፍል ውስጥ ሆን ተብሎ ኃይልን በመጠቀም የሚፈጸም ድርጊት ሲሆን፣ አስገድዶ መድፈር፣ ጠለፋ፣ ወሲባዊ ትንኮሳ፣ የሴት ልጅ ግርዛት፣ በሴቶች መነገድ፣ እና የመሳሰሉት በሴቶች ላይ የሚደረጉ የኃይል ጥቃቶች መሆናቸውን አስገንዝበዋል፡፡

በሀገራችን በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ የጾታ ጥቃቶችን ለመከላከል የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎች መኖራቸውን ጠቁመው፣ ከነዚህም መካከል የመንግስት ቁርጠኝነት፣ የሕብረተሰቡ ንቃተ ህሊና እያደገ መምጣቱ፣ ሴቶች የራሳቸውን መብት በማወቅ የመጠየቅና እድላቸውን (opportunities) የመጠቀም አቅም መጨመሩ፣ የባለድርሻ አካላትና የአጋር ድርጅቶች የጉዳዩ ባለቤት መሆናቸውና በጋራ ለመስራት ያላቸው ተነሳሽነት ማደጉ ተጠቃሽ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

የሴቶችን ጉዳይ እንዲያይ በፌዴራል ደረጃ የተሰየመው ልዩ ችሎት በሌሎች ክልሎችም ተደራሽ እንዲሆን ማድረግ፣ በሴቶች ላይ ጥቃት እንዳይፈጸም ሕብረተሰቡን ማዕከል ያደረገና ያሳተፈ የመከላከል ሥራ መስራት፣ በዚህ ዙሪያ እስካሁን ያለውን አፈጻጸም መዳሰስና ያሉትን ክፍተቶች መለየት፣ ለጥቃት ተጎጂዎች ተገቢው ትኩረት መስጠት እና የመሳሰሉ ተግባራትን ማከናወን በቀጣይ ሊተኮርባቸው የሚገቡ ጉዳዮች እንደሆኑ ወ/ሮ ሰብለ ጠቁመዋል፡፡

ዓለም አቀፍ የነጭ ሪቫን እና የዓለም ኤድስ ቀንን አስመልክቶ በተዘጋጀው ፕሮግራም ላይ የተለያዩ ትምህርት ሰጪ ግጥሞችና መነባንብ የቀረበ ሲሆን የሴቶችን ጥቃት እና ኤች.አይ ቪ/ኤድስን አስመልክቶ በቀረቡ አስተያየቶች እና ጥያቄዎች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡

   

 

የኮሚሽኑ ሰራተኞች የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀንን አከበሩ

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀንን አስመልክቶ ያዘጋጀው ሲምፖዚየም ህዳር 26 ቀን 2004 ዓ.ም. በብሔራዊ ቴያትር አዳራሽ አካሄደ ፡፡

የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን የኮሚሽኑ ሰራተኞችና የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈውን ሲምፖዚየም በንግግር ሲከፍቱ እንደገለጹት ባለፉት ሥርዓቶች የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በሠላም፣ በልማትና በዲሞክራሲ እጦት ምክንያት ለዘመናት መሠረታዊ የሆኑ ሰብዓዊ መብቶችን እና ነፃነቶችን መነፈጋቸውን ጠቁመው፣ ሕዳር 29 ቀን 1987 ዓ.ም በጸደቀው ሕገመንግስት የራሳቸውን ዕድል በራሳቸው የመወሰን መብታቸው መከበሩን እንዲሁም በኢትዮጵያ የሉአላዊ የሥልጣን ባለቤቶች ለመሆን መብቃታቸውን ገልጸዋል፡፡

በመሆኑም ሕገመንግስቱ የሰላም፣ የልማት፣ የአንድነት፣ የሉአላዊነት፣ የነጻነት መሠረት መሆኑ ግንዛቤ ማግኘት እንደሚገባው እና ሕገመንግስቱን የማወቅ፣ የማክበር እና የማስከበር  ኃላፊነት የሁሉም ዜጋ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ክቡር ኮሚሽነሩ አክለውም ሙስናን ከምንጩ ለማድረቅ እና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን በሚደረገው እንቅስቃሴ ኮሚሽኑ ትልቅ አስተዋጽኦ የሚጠበቅበት በመሆኑ ሠራተኞቹ የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴው ሠራዊትም በመሆን እንደማንኛውም ሲቪል ሰርቫንት ሕገ-መንግቱን የማወቅ፣ የማክበር እና የማስከበር ኃላፊነት የተጣለባቸው በመሆኑ ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር እና በመምራት የሙስናን መሠረት በማፍረስ የልማትና የመልካም አስተዳደር አደጋ በእጅጉ ዝቅ እንዲል የማድረግ ኃላፊነት አለብን ብለዋል፡፡

በዝግጅቱ ላይ ከሰራተኞችና ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት በቀረቡ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ላይ ሰፊ ውይይት መደረጉ ታውቋል፡፡

   

 

ኮሚሽኑ ለሁለት የስራ ሂደቶች ዳይሬክተሮችን መደበ

የፌዴራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን አቶ ገብሩ ገበየሁን ከታህሳስ 1 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮ የምርመራና ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሆነው እንዲያገለግሉ ሲመድብ፣ በሌላ በኩል የምርመራና ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ብርሃኑ ክፈተው ከተጠቀሰው ቀን ጀምሮ የሥነምግባር አውታሮች ማስተባበሪያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሆነው የሥራ ሒደቱን እንዲመሩ ተዛውረዋል፡፡

አቶ ገብሩ ገበየሁ አሁን ከተመደቡበት የሥራ ኃላፊነት በፊት በምርመራና ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት ስር በቡድን መሪነት ውጤታማ ሥራ ሲያከናውኑ የቆዩ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

እንዲሁም የኮሚሽኑ የምርመራና ዐቃቤ ሕግ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ ብርሃኑ ክፈተው የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር በነበሩበት ጊዜ በክልሉ የወጣቶች እና የሴቶች የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ንቅናቄዎችን በማደራጀትና በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴው ውጤታማ ሥራ ያከናወኑ በመሆኑ አሁን የሥነምግባር አውታሮች ማስተባበሪያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሆነው መመደባቸው በዘርፉ ያካበቱት የላቀና በተግባር የተፈተነ ልምድ ውጤታማ ሥራ ለማከናወን እንደሚረዳቸው ታምኖበታል፡፡

   
 

ኮሚሽኑ ለ146 ወጣቶች ስልጠና ሰጠ

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በአዲስ አበባ እና በክልል ከሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎችና ቀበሌዎች ለተውጣጡ 146 ወጣቶች በሥነምግባር እና በአሠራር ሥርዓት ላይ ያተኮረ ስልጠና ሰጠ፡፡

በኮሚሽኑ የስብሰባ አዳራሽ ከጥቅምት 30 - ህዳር 1 ቀን 2004 ዓ.ም እንዲሁም ከህዳር 4 – 5 ቀን 2004 ዓ.ም በሁለት ዙሮች በተሰጠው ስልጠና ወጣቶቹ በሥነምግባር እና ፀረ-ሙስና ክበባት አደረጃጀት እና የአሰራር መመሪያ ላይ ግንዛቤ እንዲጨብጡ የተደረገ ሲሆን ይህም በወረዳ እና በቀበሌ ውስጥ የሚያካሂዱትን የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ እንደሚያስችላቸው ታውቋል፡፡

በተጨማሪም ወጣቶቹ በየወረዳቸውና በየቀበሌያቸው የሚገኙ ሌሎች ወጣቶችን በማደራጀት ከትምህርት ቤት በተጨማሪም በአካባቢያቸው ከጎጂ ባህሪ እና ከተለያዩ ሱሶች በመራቅ፣ የመልካም ሥነምግባር ተምሳሌት በመሆን እንዲሁም ሙስናን በመዋጋት በልማት ንቁ ተሳትፎ ለማድረግ እንዲችሉ ስልጠናው የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማበርከት የሚያስችል እንደሆነ ለመገንዘብ ተችሏል፡፡

በሥነምግባር እና በፀረ-ሙስና ትምህርቶች ወጣቶችን በቂ ግንዛቤ በማስጨበጥ በቀጣይ ሙስና የልማትና የመልካም አስተዳደር እንቅፋት ከማይሆንበት ደረጃ ለማድረስ በሚደረገው ጥረት ንቁ ተሳታፊ እንዲሆኑ በማስቻልና የልማት እንቅስቃሴዎች ቀጥተኛ ተጠቃሚ ለማድረግ ኮሚሽኑ የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

በተመሳሳይም ኮሚሽኑ በአዲስ አበባ ከተማ ከሚገኙ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሥነ-ዜጋና የሥነ-ምግባር ክበባት ለተውጣጡ 94 መምህራንና ተማሪዎች የሥነዜጋና ሥነ-ምግባር  ክበባትን ለማጠናከር የሚረዳ የሁለት ቀናት ስልጠና በዚሁ በህዳር ወር ውስጥ መስጠቱን ለመረዳት ተችሏል፡፡

   

 

ከአራት ሚሊዮን ብር በላይ ሕገወጥ ክፍያ የፈጸሙ የእስራትና የገንዘብ ቅጣት ተወሰነባቸው

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ስልጣናቸውን አለአግባብ በመጠቀም ከአራት ሚሊዮን ብር በላይ ሕገወጥ ክፍያ ፈጽመዋል በማለት ክስ የመሰረተባቸው አራት ግለሰቦች እስከ ሰባት ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ህዳር 27 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

የኮሚሽኑ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው በቀድሞው የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን ሰራተኞች የነበሩት 1ኛ ተከሳሽ መላክ ገ/ህይወት የስዊቺንግ ዋና ክፍል ኃላፊና ሴንተራል ቢሊንግ አላርም ሴንተር (CBAC) ፕሮጀክት ኃላፊ፣ 2ኛ ተከሳሽ አበበ ጋሻው የቴክኒካል አገልግሎት ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ፣ 3ኛ ተከሳሽ አበበ በላይነህ የቴክኒካል አገልግሎት  ዋና ሥራ አስፈጻሚ እንዲሁም 4ኛ ተከሳሽ ታዬ ከበደ የቴሌኮም ኔትወርክ መምሪያ ኃላፊ በሥራ ላይ በነበሩበት ወቅት ሕገወጥ የሆነ ጥቅም ለማግኘትና ለማስገኘት እንዲሁም በመንግስት ላይ ጉዳት ለማድረስ በማሰብ ኮርፖሬሽኑ በወቅቱ ሲያሰራ የነበረው ፕሮጀክት በውሉ መሰረት ሳይጠናቀቅ ሕገወጥ ክፍያ የፈፀሙ መሆኑ ተውቋል፡፡

ግለሰቦቹ ወንጀሉን በግብርአበርነት ሊፈጽሙ የቻሉት ኮርፖሬሽኑ በወቅቱ የአገልግሎት መረጃን ከተለያዩ ሪጅኖች ወደ አንድ ማዕከል ለማሰባሰብ የሚረዳ እንዲሁም የጥገናና የኦፕሬሽን ሥራዎችን ከማዕከል ሆኖ ለመከታተል የሚያስችል ሴንተራል ቢሊንግ አላርም ሴንተር (CBAC) የተባለውን የዳታ ኔትወርክ ሲስተም ፕሮጀክት ሥራ ላይ እንዲውል ቴሌራድ ከተባለ የእስራኤል ኩባንያ ጋር እ.ኤ.አ በ2004 በገባው ውል መሰረት ፕሮጀክቱ እንዳልተጠናቀቀ እያወቁ 1ኛ ተከሳሽ ሲስተሙ አገልግሎት የማይሰጥ መሆኑን እያወቀና እንደሚሰራ በማስመሰል ለኩባንያው ክፍያ እንዲፈጸም የተለያዩ የክፍያ ሰነዶችንና ደብደቤ ወደ ክፍያ ክፍል በመላኩ እንደሆነ ለመረዳት ተችሏል፡፡ ሁለተኛ እና 3ኛ ተከሳሾች ደግሞ ለኩባንያው የርክክብ የምስክር ወረቀት በመስጠት እንዲሁም 4ኛ ተከሳሽ ክፍያ እንዲፈጸም በማዘዙ ክስ እንደተመሰረተባቸው ለመገንዘብ ተችሏል፡፡

በአጠቃላይ ተከሳሾቹ በግብርአበርነት ሥልጣንን አለአግባብ በመገልገል ላልተሰራ ዳታ ኔትወርክ ሲስተም የተሰራና አገልግሎት የሚሰጥ በማስመሰል በሕገወጥ መንገድ ለቴሌራድ ኩባንያ የብር 4,036,168 (አራት ሚሊዮን ሰላሳ ስድስት ሺህ አንድ መቶ ስድሳ ስምንት ብር) ክፍያ እንዲፈጸም በማድረግ በመንግስት ላይ ጉዳት በማድረሳቸው ክስ የተመሰረተባቸው መሆኑን የክስ መዝገቡ ያስረዳል፡፡

በመሆኑም ተከሳሾቹ የቀረበባቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃ መከላከል ባለመቻላቸው 1ኛ ተከሳሽ በ3 ዓመት ከ11 ወር ጽኑ እስራትና በብር 2,000፣ 2ኛ ተከሳሽ በ5 ዓመት ጽኑ እስራትና በብር 4,000 እንዲሁም 3ኛ እና 4ኛ ተከሳሾች እያንዳንዳቸው በ7 ዓመት ጽኑ እስራትና በብር 10,000 አንዲቀጡ ፍርድ ቤት ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

 

   

 

የኮሚሽኑ ሠራተኞች መረዳጃ ዕድር አባላት የብር 38,500 ቦንድ ገዙ

 

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሠራተኞች መረዳጃ ዕድር አባላት በሕዳሴ ግድብ ግንባታ ላይ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከት በሚችሉበት ሁኔታ ላይ ከተወያዩና የብር 38,000 (ሰላሳ ስምንት ሺህ አምስት መቶ ብር) ቦንድ ለመግዛት ውሳኔ ካሳለፉ በኋላ  በተጠቀሰው የገንዘብ መጠን ቦንድ ገዙ ፡፡

የመረዳጃ ዕድር አባላቱ ቦንድ ለመግዛት የወሰኑት ሕዳር 22 ቀን 2004 ዓ.ም በኮሚሽኑ የስብሰባ አዳራሽ ባካሄዱት ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ነው፡፡

የመረዳጃ ዕድሩ በሰኔ ወር 1995 ዓ.ም የተቋቋመ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ 77 አባላት ያሉት መሆኑንም ለመረዳት ተችሏል፡፡

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሠራተኞች የሕዳሴ ግድብ ግንባታን ለመደገፍ ሚያዚያ 3 ቀን 2003 ዓ.ም በደረጉትን ስብሰባ ላይ የወር ደመወዛቸው በአንድ ዓመት እንዲከፈል የተስማሙ ከመሆኑም በላይ ከኮሚሽኑ ሠራተኞች የገንዘብ ቁጠባና ብድር ሕብረት ሥራ ማሕበር ተቀማጭ ሂሳብ ላይ ተቀንሶ የብር 200,000 (ሁለት መቶ ሺህ ብር) ቦንድ መገዛቱ ይታወሳል፡፡

   

 

በሙስና ወንጀል የተከሰሱ 5 ግለሰቦች ተፈረደባቸው

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በሥልጣን አለግባብ መገልገል እና በሀሰተኛ ሰነዶች መገልገል የሙስና ወንጀሎች ክስ የመሰረተባቸው 5 ግለሰቦች እስከ 4 ዓመት ከአምስት ወር በሚደርስ ፅኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ህዳር 15 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

የኮሚሽኑ የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው ተከሳሽ ቴዎድሮስ ቀጀላ እና ተከሳሽ ታዬ ገ/ጊዮርጊስ በአቃቂ ቃሊት ክፍለ ከተማ አስተዳደር በቅደም ተከተላቸው የይዞታና መረጃ ቡድን መሪና የመሬት ልማት ቡድን መሪ እንዲሁም ሁለቱም በክ/ከተማው የቦታ ስፋትና ልዩነት ውሳኔ ኮሚቴ አባል ሆነው በሚሰሩበት ወቅት የአቶ መንግስተአብ ነዋይ ተወካይ የሆነችው ተከሳሽ ፀሐይ ባህታ ለጠየቀችው ቦታ የመኖሪያ ቤት ካርታ እንደማይፈቀድና ጉዳዩም ቀደም ብሎ የተዘጋ መሆኑን እያወቁ ቀያሽና የንድፍ ሰራተኛ በሆነው በሌላኛው ተከሳሽ የኔነህ ብዙነህ አማካይኝነት የቦታው ልኬት እንዲፈጸምና ካርታ እንዲዘጋጅላት ማዘዛቸው ታውቋል፡፡

ተከሳሽ የኔነህ ብዙነህ በበኩሉ ህገ-ወጥ ትዕዛዝን በመቀበል፣ በወንጀሉም ቀጥተኛ ተካፋይና ግብረአበር በመሆን የቦታ ልኬት በመፈጸምና ካርታ በማዘጋጀት በተሳሳተ መንገድ የቦታ ስፋት ልዩነት ውሳኔ ኮሚቴ እንዲወስንበት ያቀረበ ሲሆን ተከሳሽ ፀሐይ ባህታ በበኩሏ የመንግስት የሆነውን ይዞታ የወኪል አድራጊዋ የአቶ መንግስተአብ ነዋይ እንደሆነ እና በስጦታ የተገኘ በማስመሰል ከፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የተሰጠ ውሳኔ  ሳይኖር ውሳኔ የተሰጠ አስመስላ ሀሰተኛ ሰነድ በማቅረብ የማረጋገጫ ካርታ ካገኘች በኋላ ይዞታውን ለሌላ ድርጅት በብር 1,750,000(አንድ ሚሊዮን ሰባት መቶ ሃምሳ ሺህ) በመሸጥ ለግል ጥቅም በማዋሏ መከሰሷን የክስ መዝገቡ አመልክቷል፡፡

ቦታውን ህጋዊ ነው ብሎ የገዛት ድርጅት በበኩሉ ለክ/ከተማው የግንባታ ፍቃድ ጥያቄ አቅርቦ ተገቢው ማጣራት ከተደረገ በኋላ ቦታው መንገድ የሚያቋርጠውና በከፊል ግሪን ኤሪያ መሆኑ በመታወቁ በመንግስት ለድርጅቱ ግምቱ ብር 8,315,350 (ስምንት ሚሊዮን ሦስት መቶ አስራ አምስት ሺህ ሦስት መቶ ሃምሳ) የሆነ የምትክ ቦታ በመሰጠቱ ምክንያት በመንግስት ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን የክስ መዝገቡ ያስረዳል፡፡

በሌላ በኩል ቴዎድሮስ ቀጀላ እና ታዬ ገ/ጊዮርጊስ የተባሉት እነዚሁ ተከሳሾች የነበራቸውን ኃላፊነት በመጠቀም ስንታየሁ እሸቴ የተባለች ሌላኛዋ ግለሰብ የጠየቀችውን የግንባታ ፍቃድ ለመስጠት የቦታዋ ስፋት ምን ያህል እንደሆነ እንዲሁም ሌሎች ተያያዥነት ባላቸው ጉዳዮች ላይ ምንም ዓይነት ማጣራት ሳያደርጉ የቅየሳ ባለሙያው ልኬት እንዲያደርግ ትዕዛዝ በመስጠት፣ የቅየሳ ባለሙያው በበኩሉ ግለሰቧ ለይዞታው ግብር ሲከፈልበት ነበረ በማለት ያቀረበችው ሰነድ ላይ ያልሰፈረን የይዞታ መጠን “የተገኘ የይዞታ መጠን 500 ካ.ሜ፣ በልኬት የተገኘ 4,836 ካ.ሜ ነው ” በማለት የተሳሳተ መረጃ ለቦታ ስፋት ልዩነት ውሳኔ ኮሚቴ ማቅረቡና ለግለሰቧ ካርታ ማዘጋጀቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኮሚቴው አባላትም ግለሰቧን አለአግባብ ለመጥቀም በማሰብ “የገንዘብ ቅጣት ተወስኖባት  ቦታው ይጠቃለልላት” በማለት የተሳሳተ ውሳኔ በመወሰናቸው በስልጣን አለአግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ የተመሰረተባቸው ሲሆን፣ ስንታየሁ እሸቴ የተባለችው ተከሳሽ በበኩሏ ይዞታው የመንግስት መሆኑን እያወቀች ከተጠቀሱት የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተመሳጥራ ሀሰተኛ ሰነዶችን በማቅረብና በራስዋ ስም ካርታ እንዲዘጋጅ በማድረግ ቦታውን በብር 1,400,000 (አንድ ሚሊዮን አራት መቶ ሺህ) በመሸጥ ለግል ጥቅሟ ከማዋሏ የተነሳ መንግስት ከቦታው ላይ ያገኝ የነበረውን የሊዝ ዋጋ ብር 4,862,598 (አራት ሚሊዮን ስምንት መቶ ስልሳ ሁለት ሺህ አምስት መቶ ዘጠና ስምንት) በማጣቱ መንግስት ላይ ጉዳት መድረሱ ተጠቁሟል፡፡

በመሆኑም ተከሳሾቹ ኮሚሽኑ በክስ ሂደቱ ያቀረበባቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን መከላከል ባለመቻላቸውና በፈጸሙት የሙስና ወንጀል ሙሉ ተካፋይ በመሆናቸው ተከሳሽ ቴዎድሮስ ቀጀላ ፣ ተከሳሽ ታዬ ገ/ጊዮርጊስ እና ተከሳሽ የኔነህ ብዙነህ እያንዳንዳቸው በ3 ዓመት ከ11 ወር ፅኑ እስራትና በብር 2,000 እንዲቀጡ የተወሰነ ሲሆን ተከሳሽ ስንታየሁ እሸቴ እና ተከሳሽ ፀሐይ ባህታ ደግሞ እያንዳንዳቸው በ4 ዓመት ከ5 ወር ፅኑ እስራትና በብር 20,000 እንዲቀጡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

   

 

በከባድ የእምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል የተከሰሰ ግለሰብ በፅኑ እስራትና በገንዘብ ተቀጣ

(ፌ.ስ.ፀ.ሙ.ኮ) የፌዴራል የሥነምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በከባድ እምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል ክስ የመሰረተበት ግለሰብ በ8 ዓመት ከ5 ወር ፅኑ እስራትና በ30 ሺህ ብር እንዲቀጣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ህዳር 15 ቀን 2004 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

ኮሚሽኑ አቶ ደምስ ጠይም መሃመድ በተባለው ግለሰብ ላይ የመሰረተው ክስ እንደሚያስረዳው ተከሳሹ ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለማግኘት በማሰብ የመንግስት የልማት ድርጅት በሆነው በባቱ ኮንስትራክሽን አክሲዮን ማህበር ውስጥ የመለዋወጫ ዕቃዎች ግምጃ ቤት ሰራተኛ ሆኖ በሚሰራበት ወቅት ከሐምሌ 1 ቀን 2000 ዓ.ም እስከ ሰኔ 30 ቀን 2001 ዓ.ም ድረስ በስራው ምክንያት ከተረከባቸው የኮንስትራክሽን መሳሪያዎችና የቀላልና የከባድ መኪኖች መለዋወጫ እቃዎች መካከል ግምታቸው ብር 253,515/ሁለት መቶ ሀምሳ ሦስት ሺህ አምስት መቶ አስራ አምስት ብር / የሚያወጡና ሌሎች ዋጋቸው ያልታወቀ 174(አንድ መቶ ሰባ አራት) የሚሆኑ የተለያዩ ዕቃዎችን ለግል ጥቅሙ አውሏል የሚል ነው፡፡

በመሆኑም ግለሰቡ በክስ ሂደቱ የቀረበበትን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን መከላከል ባለመቻሉ ፍርድ ቤቱ ከላይ በተጠቀሰው የፅኑ እስራትና የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

   
 

ከ56 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የመንግስት መሬት ለግል ጥቅማቸው ያዋሉ ሁለት ግለሰቦች ተፈረደባቸው

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከ56 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት  የመንግስት መሬት ለግል ጥቅም አውለዋል በማለት  ክስ በመሰረተባቸው ሁለት ግለሰቦች ላይ የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 1ኛ ወንጀል ችሎት ሕዳር 12 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት እያንዳንዳቸው በ10 ዓመት ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

የቅጣት ውሳኔው የተላለፈባቸው ተከሳሾች ቆንጂት ደስታ እና መኮንን ወለላው የተባሉ በንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ ግለሰቦች ሲሆኑ የአዲስ አበባ መስተዳደር ቀደም ብሎ በህጋዊ መንገድ ለተደራጁና በተለያዩ ምክንያቶች ቦታ ያላገኙ ነባር የመኖሪያ ቤት ማህበራት ቦታ እንዲያገኙ በ1990 ዓ.ም ባደረገው የጥሪ ማስታወቂያ መሠረት ተከሳሾቹ «የህይወት በር የመኖሪያ ቤት ሕብረት ሥራ ማሕበር» በመባል የሚታወቅ ማህበር ፋይልና ሰነዶች በህገ-ወጥ መንገድ ከመስሪያ ቤት እንዲወጣላቸው በማድረግ ራሳቸውን የማህበሩ ሊቀመንበርና ፀሐፊ በማድረግ እንዲሁም ማህተም በማስቀረጽና ብዛታቸው 202 የሆኑ አባላት ስም ዝርዝር በመያዝና ሌሎች ሐሰተኛ ሰነዶችን በማዘጋጀት በማህበሩ ስም ፋይል ማስከፈታቸውን የክስ መዝገቡ አመልክቷል፡፡

በመሆኑም ተከሳሾቹ ማህበሩ በሕጋዊ መንገድ ተደራጅቶ ቦታ ባልተሰጠበት ሁኔታ ግምቱ ብር 56,027,689.60 (ሃምሳ ስድስት ሚሊዮን ሃያ ሰባት ሺህ ስድስት መቶ ሰማንያ ዘጠኝ ብር ከስድሳ ሳንቲም) የሚገመት 32,320 ካሬ ሜትር የመንግስት መሬት በህገ-ወጥ መንገድ በወረራ በመውሰድና ሸጠው ለግል ጥቅማቸው በማዋላቸው በመንግስት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማድረሳቸው መከሰሳቸው ታውቋል፡፡

በተከሳሾቹ ላይ የተመሰረተው የመጀመሪያ ክስ እንደሚያመለክተው ሁለቱም ተከሳሾች በማህበሩ ስም ያቀረቡዋቸው ሰነዶች ሁሉ ህጋዊ እንደሆኑና የመንግስት ተቋማት ህጋዊ በሆነ ማህበር ላይ ሁከት የፈጠሩ በማስመሰል ሐሰተኛውን ነገር እውነት አስመስለው ለከተማ ቦታ ማስለቀቅ ይግባኝ ሰሚ ጉባኤ አቤቱታ አቅርበው ጉባኤውን በማሳሳት ያለአግባብ የመሬት ካርታ እንዲሰጣቸው በማስደረጋቸው በከባድ አታላይነት የሙስና ወንጀል ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡

በተከሳሾቹ ላይ በተጨማሪ የተመሰረተው ሁለተኛ ክስ እንደሚያስረዳው ሁለቱም ተከሳሾች ቀደም ሲል በህጋዊ መንገድ ተቋቁሞ የነበረውን «የህይወት በር የመኖሪያ ቤት ሕብረት ሥራ ማህበር» መጀመሪያ በህጋዊ መንገድ በተመሰረተበት ወቅት የነበረውን የአባላት ስም ዝርዝር ከፋይሉ ውስጥ በማጥፋትና በወቅቱ የማህበሩ የማደራጃ ኃላፊ የነበረውን ግለሰብ የሥራ ኃላፊነትና የስም ቲተር እንዲሁም ፊርማ በሐሰት በመጠቀም፣ ቀኑና ወሩ በውል ባልተወቀበት በ1994 ዓ.ም በማህበሩ ስም የሽንሻኖ፣ የሳይት ፕላን፣ የሎኬሽን ማፕ፣ የሶፍራቶፕ፣ የዝርዝር ፕላን፣ የቶፖሎጂ ሰነዶችን በሐሰት ከማዘጋጀታቸውም በተጨማሪ ቤት የመሸጥ ህጋዊ ውክልና የተሰጣቸው በማስመሰል ህገ-ወጥ ሰነዶችን መንግስታዊ ሰነዶች አስመስለው በማዘጋጀታቸው መንግስታዊ ሰነዶችን ወደ ሀሰት በመለወጥ የሙስና ወንጀል ተከሰዋል፡፡

ተከሳሾቹ በሁለቱም ክሶች በፈጸሙት የከባድ አታላይነት እና መንግስታዊ ሰነዶችን ወደ ሐሰት የመለወጥ የሙስና ወንጀሎች ውስጥ ሙሉ ተሳታፊና በውጤቱም ሙሉ ተከፋዮች ስለመሆናቸው ኮሚሽኑ ያቀረበባቸውን የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች መከላከል ባለመቻላቸው ከላይ የተጠቀሰው የእስር ቅጣት ተላልፎባቸዋል፡፡

   

 

በ15 ሺህ ብር ሐሰተኛ የመንጃ ፈቃድ ሲሰጡ የነበሩ የሥራ ኃላፊዎችና ሙያተኞች እጅ ከፍንጅ ተያዙ

አዲስ አበባ ደቡብ ዞን ትራንስፖርት ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን ለገሰ ጠው እና የጽ/ቤቱ የመንጃ ፈቃድ እድሳት ባለሙያ አቶ ዘላለም አብይ አየለ እንዲሁም በሕገ-ወጥ ድርጊት ተባባሪ የሆነ እንድ የፌደራል ፖሊስ አባል ለአንድ ግለሰብ ሐሰተኛ የመንጃ ፈቃድ ለመስጠት በትራንስፖርት ጽ/ቤቱ15ሺህ ብር ጎቦ ሲቀበሉ ህዳር 11 ቀን 2004 ዓ.ም በፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እጅ ከፍንጅ ተያዙ፡፡

ግለሰቦቹ ሊያዙ የቻሉት የአዲስ አበባ ደቡብ ዞን ትራንስፖርት ጽ/ቤት ሐሰተኛ የመንጃ ፈቃድ እንደሚሰጥ በሕብረተሰቡ ውስጥ የሚነገረውን መነሻ በማድረግ ኮሚሽኑ ለአንድ ሳምንት ባደረገው ክትትል ነው፡፡

ግለሰቦቹ እንዲህ ዓይነቱን ሕገ-ወጥ ድርጊት ሲፈጽሙ የነበረው የራሳቸውን መዋቅር በመፍጠር ሲሆን ለሕገ-ወጥ ድርጊታቸው በፈጠሩት በዚህ መዋቅራቸው መሰረት የፌደራል ፖሊስ አባል የነበረው ኮንስታብል አብርሃይ ዘርሁን በርሄ ከክልሎችና ከአዲስ አበባ ከተማ ሰዎችን በማግባባትና የድለላ ሥራዎችን በመስራት ሐሰተኛ የመንጃ ፈቃዱን ለመስጠት የሚረዱ መረጃዎችን ከግለሰቦቹ በማሰባሰብና አደራጅቶ በማዘጋጀት ለተጠቀሰው የትራንስፖርት ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ እና ለመንጃ ፈቃድ እድሳት ባለሙያው በማቀባበል እንደነበረ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ሥራ አስኪያጁ እና የመንጃ ፈቃድ እድሳት ባለሙያው  በበኩላቸው ሕብረተሰቡን እንዲያገለግሉ የተሰጣቸውን የመንግስት ኃላፊነት ወደጎን በመተው ከተጠቀሰው የፌደራል ፖሊስ አባል የሚመጣላቸውን መረጃ በመጠቀምና ሐሰተኛ የመንጃ ፈቃድ የሚሰጣቸው ግለሰቦች ከዚህ በፊት የመንጃ ፈቃዱን አውጥተው የጠፋባቸው በማስመሰል በመ/ቤቱ የኮምፒውተር ሲስተም ውስጥ ካስገቡ በኋላ ከብር 15 ሺህ እስከ 20 ሺህ የሚደርስ ገንዘብ በመቀበል የተፈለገውን የመንጃ ፈቃድ ደረጃ ለግለሰቦቹ በምትክነት የተሰጠ በማስመሰል ሕገ-ወጥ ሥራ ሲሰሩ እንደነበር በወቅቱ ከተያዙ መረጃዎች ለመረዳት ተችላል፡፡

በአሁኑ ወቅትም ኮሚሽኑ በተፈጸመው ህገ-ወጥ ድርጊት ዙሪያ ተጨማሪ መስረጃዎችን አሰባስቦ በተጠርጣሪዎቹ ላይ ክስ ለመመስረት በሂደት ላይ ይገኛል፡፡

   

 

የቀድሞው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፕሬዝዳንት ከሌሎች የሙስና ወንጀል ተጠርጣሪዎች ጋር ፍርድ ቤት ቀረቡ

የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ ያረጋል አይሸሹም ከሌሎች ስድስት የሙስና ወንጀል ተጠርጣሪዎች ጋር ጥቅምት 21 ቀን 2004 ዓ.ም በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ክስ ተመሰረተባቸው፡፡

ከ1ኛ ተከሳሽ ከአቶ ያረጋል አይሸሹም ጋር በኮሚሽኑ ክስ የተመሰረተባቸው የክልሉ የትምህርት ቢሮ ኃላፊ የነበሩት 2ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ ሂካ፣ የጌድዮን ደመቀ አማካሪ ድርጅት ባለቤትና ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት 3ኛ ተከሳሽ አቶ ጌድዮን ደመቀ፣ በግል ሥራ የሚተዳደሩት 4ኛ ተከሳሽ አቶ አሰፋ ገበየሁ፣ የጋድ ኮንስትራክሽን ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት 5ኛ ተከሳሽ አቶ ገዛኸኝ አድገህ፣ የኮለን ኮንስትራክሽን ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ የሆኑት 6ኛ ተከሳሽ አቶ መክብብ ሞገስ እና በንግድ ሥራ የሚተዳደሩት 7ኛ ተከሳሽ አቶ ኃይለገብርኤል ሂካ  ናቸው፡፡

ኮሚሽኑ ዐቃቤ ሕግ ከዚህ በላይ ከ1ኛ- 4ኛ በተጠቀሱት ተጠርጣሪዎች ላይ የመሰረተው ክስ እንደሚያመለክተው ተከሳሾቹ በሕገ-ወጥ መንገድ በስውር እና በመመሳጠር ሕገ-ወጥ የሆነ የጥቅም ግንኙነት በመፍጠር የማይገባ ጥቅም ለማግኘትና በመንግስት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ አስበው የግልገል በለስ መምህራን ኮሌጅ፣ የጣና በለስ የሴቶች አዳሪ ትምህርት ቤት እና የአሶሳ ሙያና ቴክኒክ ማሰልጠኛ ተቋምን ከፌዴራል መንግስት በተሰጠ የበጀት ድጎማ እና በክልሉ በተመደበ በጀት በ1998 ዓ.ም እና ለማስገንባት በተደረገው እንቅስቃሴ የጨረታውን ሒደት ማዛባታቸው ተገልጿል፡፡

በዚህ መሠረት 1ኛ ተከሳሽ አቶ ያረጋል አይሸሹም እና 2ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ ሂካ ለፕሮጀቶቹ የተመደበው ገንዘብ ከፍተኛ መሆኑን እያወቁ በክልሉ የግዥ መመሪያ መሠረት ግልጽ ጨረታ በማውጣት የተሻሉ ተወዳዳሪዎችን በመጋበዝ ማጫረት እና ማሰራት ሲገባቸው የሶስቱንም ፕሮጀክቶች ጨረታ በሕገ-ወጥ መንገድ ለጌድዮን ደመቀ አማካሪ ድርጅት ሰጥተዋል፡፡

በቅደም ተከተል 3ኛ እና 4ኛ ተከሳሽ የሆኑት አቶ ጌድዮን ደመቀ እና አቶ አሰፋ ገበየሁ  ከዲዛይን ስራው በጠቅሉ 250‚000 (ሁለት መቶ ሀምሳ ሽህ ብር) እንዲሁም ለቁጥጥር እና ለኮንትራት አስተዳደር ከሚከፈለው ደግሞ በየወሩ 10‚000 (አስር ሺህ ብር) ለ1ኛ እና ለ2ኛ ተከሳሾች ሊከፍሉ በሚስጢር በመደራደር 1ኛተከሳሽ በክልሉ የነበራቸውን ከፍተኛ ስልጣን ያለአግባብ በመጠቀም የሶስቱንም ፕሮጀክቶች ስራ “ስራው አስቸኳይ ነው” በሚል ከግዢ መመሪያ ወጭ በውስን ጨረታ ፕሮጀክቶችን ለመስራት ደረጃው የማይፈቅድትን የጌድዮን ደመቀ አማካሪ ድርጅት አሸናፊ እንዲሆን በማድረግ ከዚሁ ድርጅት 1ኛ ተከሳሽ ብር 50‚000፣ 2ኛ ተከሳሽ ብር 75‚000 መቀበላቸው በክሱ ላይ ተመልክቷል፡፡

በተመሳሳይም 2ኛ ተከሳሽ አቶ ሀብታሙ ሂካ የአሶሳ ሙያና ቴክኒክ ማሰልጠኛ ተቋምን ዲዛይን፣ የኮንትራት አስተዳደርና የቁጥጥር ስራ ለማከናወን የተጣበበ ጊዜ በመወሰንና በሕገወጥ መንገድ የጌድዮን ደመቀ አማካሪ ድርጅት አሸናፊ እንዲሆን በማድረግ ከዚሁ ድርጅት ጋር ውል የተዋዋሉ ከመሆኑም በላይ በ13 ወራት ያልቃል የተባለለት የሶስቱ ፕሮጀክቶች የቁጥጥርና የኮንትራት አስተዳደር ስራ ተከሳሾች ባላቸው የጥቅም ግንኙነት ምክንያት እስካሁን ሊጠናቀቅ ካለመቻሉም በላይ ከውሉ ውጭ በሶስቱም ፕሮጀክቶች ስም ለጌድዮን ደመቀ አማካሪ ድርጅት በድምሩ ብር 2‚832‚450.00 ተጨማሪ ክፍያ እንዲፈጸም ማድረጋቸው በክሱ ላይ ተመልክቷል፡፡

አምስተኛ ተከሳሽ የጋድ ኮንስትራክሽን ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ የግልገል በለስ መምህራን ኮሌጅን እና የጣና በለስ የሴቶች አዳሪ ትምህርት ቤትን የግንባታ ሥራ በህገወጥ መንገድ ለማግኘት ለ1ኛ እና 2ኛ ተከሳሾች ብር 3‚000‚000.00 (ሦስት ሚሊዮን ብር) ለመስጠት በሚስጢር ባደረጉት ድርድር አማካኝነት የሁቱንም ፕሮጀክቶች ግንባታ ለማከናወን በህገወጥ መንገድ ውል መረከባቸው በክሱ ላይ ተመልክቷል፡፡

ስራው ውል ከተገባበት ከሚያዚያ ወር 1998 ዓ.ም ጀምሮ ከ13-18 ወራት ውስጥ ያልቃል የተባለው የሁለቱ ፕሮጀክቶች የግንባታ ሥራ ተከሳሾች ባላቸው የጥቅም ግንኙነት ምክንያት እስካሁን ሊጠናቀቅ ካለመቻሉም በላይ ከውሉ ውጭ ለግልገል በለስ መምህራን ኮሌጅ 2‚528‚312.51፣ ለጣና በለስ የሴቶች አዳሪ ትምህርት ቤት ብር 1‚766‚838.65 በድምሩ ብር 4‚295‚151.16 (አራት ሚሊዮን ሁለት መቶ ዘጠና አምስት ሺህ አንድ መቶ ሀምሳ አንድ ብር ከ16/100) ተጨማሪ ክፍያ ማስወጣቱም ተጠቅሷል፡፡

ስድስተኛ ተከሳሽ አቶ መክብብ ሞገስ የኮለን ኮንስትራክሽን ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ በመሆን በሚሰሩበት ጊዜ የማይገባ ጥቅም ለማግኘትና በመንግስት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ አስበው የአሶሳ ሙያና ቴክኒክ ማሰልጠኛ ተቋምን ለመገንባት ለ1ኛ እና ለ2ኛ ተከሳሾች ብር 700‚000 (ሰባት መቶ ሺህ ብር) ለመስጠት በሚስጢር ባደረጉት ድርድር የዚህን ፕሮጀክት የግንባታ ስራ ታህሳስ 3 ቀን 1999 ዓ.ም በመረከባቸው ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡

ሰባተኛ ተከሳሽ አቶ ኃይለገብርኤል ሂካ በ1996 ዓ.ም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ከተመረቁ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ በጋ አግሮ ኢንዱስትሪ ኃ/የተ/የግል ማህበር በሚል ስያሜ በ10 ሚሊዮን ብር የእርሻ ኢንቨስትመንት እና በ10 ሚሊዮን ብር ዩፎሪያ ኢንተርናሽናል ቢዝነስ ኃ/የተ/የግል ማህበርተሰኘ የእብነበረድ ማምረቻ ማፍራት የሚያስችላቸው ምንም አይነት ህጋዊ ሁኔታ ሳይኖር ከ2ኛ ተከሳሽ ከአቶ ሀብታሙ ሂካ ጋር በሚስጢር የነዚህ ድርጅቶች ባለቤት ሆነው መገኘታቸውን ኮሚሽኑ የመሠረተው ክስ ያስረዳል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ አቶ ያረጋል አይሸሹም እና አቶ ሀብታሙ ሂካ የመንግሥት ተቀጣሪ ቢሆኑም በሕጋዊ መንገድ ሲያገኙት ከነበረው ገቢ በላይ በርካታ ሀብት ያፈሩ መሆኑ ተጠቅሶ ክስ የተመሰረተባቸው ሲሆን፣ ፍርድ ቤቱ ጥቅምት 21 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ኮሚሽኑ በተከሳሾች ላይ ቅድመ ክስ መስርቶ ሕዳር 12 ቀን 2004 ዓ.ም እንዲቀርብ፣ ተከሳሾችም እስከዚያው ድረስ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡

   
 

ኮሚሽኑ ስምንት ሺህ ብር ጉቦ የተቀበለውን ግለሰብ እጅ ከፍንጅ ያዘ

/ፌ.ሥ.ፀ.ሙ.ኮ 06/03/2004/ የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በልደታ ክፍለ ከተማ በወረዳ 1 አስተዳደር ጽሕፈት ቤት የመሬት አስተዳደርና የግንባታ ፈቃድ አሰጣጥ ኦፊሰር የሆነው እንደሻው ገብረ ሕይወት ኃይሌ ከአንድ ባለጉዳይ ብር 8000.00 (ስምንት ሺህ ብር) ጉቦ ሲቀበል ሕዳር 6 ቀን 2004 ዓ.ም እጅ ከፍንጅ ያዘ፡፡

ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ስር ለማዋል ከተካሄደው ኦፕሬሽን ጋር በተያያዘ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው አንድ ባለጉዳይ ነባር ይዞታቸውን በተመለከተ አስፈላጊውን ማስረጃ በመያዝ ካርታ እንዲዘጋጅላቸው ለልደታ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ጽሕፈት ቤት ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡

የልደታ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ጽሕፈትም በጥያቄው ላይ አስተያየት እንዲሰጥበት ጉዳዩን የባለጉዳዩ ይዞታ ወደሚገኝበት የክፍለ ከተማው የወረዳ 1 አስተዳደር ጽሕፈት ቤት ይመራዋል፡፡

ተጠርጣሪውም ባለበት የሥራ ኃላፊነት የባለጉዳዩን ይዞታ በአካል ሄዶ ካረጋገጠ በኋላ በይዞታው ወሰን ላይ የሌላ ሰው ንብረት የሚገኝ በመሆኑ ለባለጉዳዩ ካርታው ሊዘጋጅላቸው እንደማይችል ገልጾ “ካርታው እንዲሰራ ከተፈለገ በካርታው አሰጣጥ ላይ በጋራ ለምንወስን ሰዎች የሚከፋፈል ብር 8000.00 ይሰጠኝ” በማለት ባለጉዳዩን ይጠይቃል፡፡

ባለጉዳዩም የተጠቀሰው የገንዘብ መጠን እንደሚበዛና ተጠርጣሪው አስተያየት በማድረግ እንዲቀንስላቸው ቢደራደሩም እምቢተኝነቱን ይገልጻል፡፡ 

ይህ በዚህ እንዳለ ባለጉዳዩ መረጃውን ለኮሚሽኑ በማቅረባቸው ተጠርጣሪው ከላይ የተጠቀሰውን የገንዘብ መጠን ብሔራዊ ቴያትር አጠገብ በሚገኝ የመዝናኛ ቦታ ሲቀበል የኮሚሽኑ ክትትል ሰራተኞች እጅ ከፍንጅ ሊይዙት ችለዋል፡፡

ኮሚሽኑ በተጠርጣሪው ላይ ክስ ለመመስረትም ተጨማሪ ምርመራ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡

 

   
 

ኮሚሽኑ 150‚000 ብር ጉቦ የተቀበለውን እጅ ከፍንጅ ያዘ

የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ዋና መስሪያ ቤት የክትትል እና ጥበቃ ሠራተኛ የሆነው ዳንኤል አስራት ዘውዱ ጥቅምት 27 ቀን 2004 ዓ.ም ብር 150‚000 ጉቦ ሲቀበል በፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እጅ ከፍንጅ ተያዘ፡፡

በቁጥጥር ስር የዋለው ተጠርጣሪ፣ “ወርልድ የጉዞና አስጎብኚ ድርጅት” ቀደም ሲል ለስራ ጉዳይ ከቀረጥ ነጻ ወደአገር ውስጥ ያስገባውን ተሽከርካሪ ተገቢ ላልሆነ ስራ በማዋሉ ተሽከርካሪው የተወረሰበትን የዚህ በፊት አጋጣሚን መሠረት በማድረግ፣ አሁንም “ሌሎች የድርጅቱን ተሽከርካሪዎች ተገቢ ላልሆነ ስራ ስለማዋላችሁ አስፈላጊውን መረጃ እየሰባሰብን በመሆኑ እነዚህ መረጃዎች ግልጽ እንዳይወጡባችሁ ብር 150‚000 ስጡኝ” በሚል ለድርጅቱ ጥያቄ ያቀርባል፡፡

በዚህ መሠረት ከአስጎብኚ ድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ ጋር ድርድር ውስጥ ይገባል፡፡ ይሁንና መረጃው በአስጎብኚ ድርጅቱ አማካኝነት ለኮሚሽኑ በመድረሱ ተጠርጣሪው ካዛንችስ አካባቢ በሚገኘው የፌደራል ሠራተኛና ማሕበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ፊት ለፊት 150‚000 ብር ሲቀበል የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን መርማሪዎች እጅ ከፍንጅ ሊይዙት ችለዋል፡፡

ኮሚሽኑ ተጠርጣሪውን ወደ ሕግ ለማቅረብ ተጨማሪ ምርመራዎችን እያካሄደ ይገኛል፡

   
 

የደቡብ ሱዳን የፀረ-ሙስና ተቋም የልዑካን ቡድን

በኮሚሽኑ የሥራ ጉብኝት አደረገ

በደቡብ ሱዳን የፀረ-ሙስና ተቋም ምክትል ሊቀመንበር በክቡር ጆኒ ሳቬሪዮ አይክ የሚመራና ስድስት አባላት ያሉት የልዑካን ቡድን በፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከጥቅምት 20-24 ቀን 2004 ዓ.ም የሥራ ጉብኝት አደረገ፡፡

የልዑካን ቡድኑ አባላት በሥራ ጉብኝታቸው ስለፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን አመሰራረት እንዲሁም ኮሚሽኑ የሥነምግባር ትምህርትን በማስፋፋት፣ ሙስናን በመካከል፣ በሙስና ወንጀል ተጠርጣሪዎች ላይ ስለሚያካሒደው ምርመራና ክስ አቀራረብ፣ ስለጥናትና ለውጥ ሥራ አመራር የሥራ ኃላፊነት፣ በሥነምግባር አውታሮች እንቅስቃሴና በሀብት ማሳወቅና ምዝገባ አሠራር በየዳይሬክቶሬቶቹ የሥራ ኃላፊዎች ዝርዝር ማብራሪያ ቀርቦላቸዋል፡፡

በሥራ ጉብኝቱ ማጠቃለያ ላይ የልዑካን ቡድኑ መሪ ክቡር ጆኒ ሳቬሪዮ አይክ ባደረጉት ንግግር በቆይታቸው በአገራቸው የፀረ-ሙስና ተቋም ተግባራዊ ሊያደርጓቸው የሚገቡ የተለያዩ አሰራሮችን መቅሰማቸውን ገልፀው፣ በተለይ በኢትዮጵያ መንግስትና በኮሚሽኑ ሰራተኞች በኩል ሙስናን ለመዋጋት ያለውን ተነሳሽነትና ቁርጠኝነት ሳያደንቁ እንደማያልፉ ገልፀዋል፡፡

በፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በየደረጃው ያሉ የሥራ ኃላፊዎች ከበታች ሰራተኞች ጋር ያላቸው መልካም ግንኙነትም ትኩረታቸውን እንደሳበው አስረድተዋል፡፡

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን  ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር የልዑካን ቡድኑ አባላትም ሆኑ ሌሎች የደቡብ ሱዳን ሕዝቦች በኢትዮጵያ እንደጎረቤት አገር ህዝቦች ሳይሆን እንደወንድም የሚታዩ መሆኑን ገልጸው፣ የደቡብ ሱዳን የፀረ-ሙስና ተቋም በቅርቡ የተቋቋመ እንደመሆኑ መጠን በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴው ዙሪያ ከሌሎች ልምድ ካላቸው አገሮች ለመማር ሰፊ ዕድል ያለው መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡

በውይይቱ ማጠቃለያ ላይም የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የሥራ ኃላፊዎች በደቡብ ሱዳን የፀረ-ሙስና ተቋም የሥራ ጉብኝት በማድረግ በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴው ዙሪያ ያላቸውን ልምድ እንዲያካፍሉ ግብዣ ያቀረቡላቸው ሲሆን ክቡር አቶ አሊ ሱለይማንም ግብዣውን የተቀበሉት መሆኑንና ወደፊት አመች በሆነ ጊዜ የሥራ ጉብኝቱን  እንደሚደርጉ ቃል ገብተዋል፡፡

   

 

የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ሞጁሎችን ለማሻሻል የሚረዳ ውይይት ተካሔደ

በመንግሥት መስሪያ ቤቶች እና የልማት ድርጅቶች ለሚገኙ ሠራተኞች እንዲሁም ለህብረተሰቡ በሥነምግባር እና በፀረ-ሙስና ትምህርቶች ዙሪያ ላለፉት አራት ዓመታት የፊት ለፊት ሥልጠና ሲሰጥበት የቆየውን የሥልጠና ሞጁል ለማሻሻል እንዲቻል ለውጥ ሊደረግባቸው በሚገቡ ጭብጦች ዙሪያ ግብዓት ለማሰባሰብ የሚረዳ የሁለት ቀን ውይይት ተካሔደ፡፡

በፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የስብሰባ አዳራሽ ከጥቅምት 16-17 ቀን 2004 ዓ.ም በተካሔደው በዚህ የውይይት መድረክ ላይ ተሰብሳቢዎቹ በሙስና ጽንሰ-ሐሳብ፣ በሥነምግባር መርሆዎችና የሥነምግባር ደንብ አዘገጃጀት፣ በሙስና ወንጀሎች፣ ጥፋተኞችን ለመቅጣትና በሙስና ያገኙትን ንብረት ለመውረስ በሚያስችል ሥርዓት በመዘርጋት ሙስናን የመከላከል ስልት፣ በሙስና መከላከል ስትራቴጅዎች፣ በሙስና መከላከያ ስልቶች እንዲሁም የአሰራር ሥርዓት ጥናት በማካሄድ የሚከናወን የማማከር አገልግሎት ላይ ኮሚሽኑ ስልጠና ሲሰጥባቸው የቆዩ ሰባት ሞጁሎች ስለሚሻሻሉበት ሁኔታ የሀሳብ ልውውጥ ተደርጓል፡፡

በውይይቱ ላይም ከተለያዩ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ የሥነዜጋና የሥነምግባር ክበባት አስተባባሪዎች፣ ሞጁሉን በመጠቀም የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ትምህርት በመስጠት የተሻለ አፈፃፀም ካሳዩ የሥነምግባር መኮንኖች እንዲሁም ከኮሚሽኑ የተለያዩ ዳይሬክቶሬቶች የተውጣጡ 29 ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡

ተሰብሳቢዎቹ ለአራት ቡድኖች ተከፍለው ሞጁሎችን ከተለያዩ መመዘኛዎች አንጻር ከገመገሙ በኋላ ሊሻሻሉ በሚገባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ስምምነት ላይ የደረሱባቸውን ነጥቦች በተመለከተ ሁሉም ተሰብሳቢዎች በተገኙበት የጋራ ውይይት ተደርጎበታል፡፡

የስልጠና ሞጁሎችን ማሻሻል ያስፈለገው ሞጁሎቹ ሥራ ላይ በቆዩባቸው አራት ዓመታት ውስጥ ከታዩ ልዩ ልዩ ለውጦች አንጻር መረጃዎችን ወቅታዊ ለማድረግና በተጠቀሰው ጊዜ በማስተማር ሒደት ያጋጠሙ ችግሮችን መሠረት በማድረግ ማስተካከያ ለማድረግ መሆኑንም ለመረዳት ተችሏል፡፡

   

 

በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሊኖረው ስለሚገባ ድርሻ ውይይት ተካሔደ

የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን መልካም ሥነምግባርን ለማስፋፋትና ሙስናን ለመከላከል በሚያደርገው ጥረት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ጨምሮ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የሌሎች አካላት ድርሻ ምን ሊሆን እንደሚገባ የሚያመላክት ውይይት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥቅምት 15 ቀን 2004 ዓ.ም ተካሔደ፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 16 የቋሚ ኮሚቴዎች አባላት በተገኙበት በተካሔደው በዚህ ውይይት ላይ የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር ክቡር አቶ አዲሱ መንግስቱ በሰጡት ማብራሪያ ኮሚሽኑ ዓላማውን ከማስፈፀም አንጻር ከሌሎች ተቋማት ጋር ስለሚኖር ቅንጅታዊ አሰራር፣ ሙስናንና ብልሹ አሠራርን ከመከላከል አንፃር የመንግስት ተቋማት ሊጫወቱት ስለሚገባ ሚና፣ በዚህ ዙሪያ ስለሚታዩ ውስንነቶችና የወደፊት አቅጣጫ እንዲሁም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና የመንግስት ተቋማት በዚህ ረገድ ስለሚኖራቸው ድርሻ የሚያመላክቱ ሀሳቦችን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

ክቡር ም/ኮሚሽነሩ ለውይይቱ መነሻ እንዲሆን ለቋሚ ኮሚቴ አባላቱ ባደረጉት ማብራሪያ የኮሚሽኑን ዓላማዎችና የማስፈፀሚያ ዘዴዎች፣ ከተቀናጀ የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ አኳያ የኮሚሽኑ የእስከዛሬ ጉዞና በቀጣይ ሊታዩ ስለሚገባቸው ጉዳዮች፣ ሙስናን ከመከላከል አንፃር የመንግስት መስሪያ ቤቶች ወይም ድርጅቶች የበላይ ኃላፊዎች ኃላፊነት እና ተቋማት ይህን ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ለመወጣት እንዲችሉ ስለተቀመጠ አደረጃጀት ጨምረው አስገንዝበዋል፡፡

በተጨማሪም የሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች ዓላማዎችና ተግባራት፣ ለሥነምግባር መከታተያ ክፍሎቹ ምቹ የሥራ ሁኔታ መፍጠርን በሚመለከት ለተቋማት ስለተሰጡ ኃላፊነቶች እና ተቋማት ይህን ኃላፊነት ለመወጣት ሊዘረጉት ስለሚገባ አሰራር፣ በመንግስት ተቋማት ሙስናን የመላከል ኃላፊነትን ከመወጣት አንጻር ስለታዩ ችግሮችና ሙስናንና ብልሹ አሠራርን ከመከላከል አንፃር ሊሻሻሉ ስለሚገባቸው ጉዳዮች እንዲሁም የመንግሥት ተቋማትን የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ ከማጠናከር አንፃር ከሕዝብ ተወካዮ ምክር ቤት በሚጠበቁ ድጋፎች ዙሪያ በዝርዝር አስረድተዋል፡፡

የቀረበውን ማብራሪያ ተከትሎ ከቋሚ ኮሚቴዎቹ አባላቱ በኮሚሽኑ አሠራር ዙሪያ የተለያዩ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን ያቀረቡ ሲሆን፣ በተለይ ስለኮሚሽኑ ተደራሽነት፣ ሙስናን በመታገል ዙሪያ የላቀ አፈጻጸም የሚሳዩ የሥራ ኃላፊዎችን ለማበረታታት ስለሚደረግ ጥረት፣ ስለሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች አደረጃጀትና የሥራ ነጻነት፣ ጥቆማ ለሚያቀርቡ ሰዎች ስለሚደረግ ከለላና በሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ ለቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

   

 

የቀድሞው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፕሬዝዳንት በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ዋሉ

የቤንሻንጉል ጉሙዝ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዚዳንት የነበሩት አቶ ያረጋል አይሸሹም በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው ጥቅምት 9 ቀን 2004 ዓ.ም በፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት አባልና የህብረት ስራ ማህበራት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር የሆኑት አቶ ያረጋል አይሸሹም በቁጥጥር ስር የዋሉት የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የተጠርጣሪው ያለመከሰስ መብት እንዲነሳ ለምክር ቤቱ ያቀረበውን ጥያቄ መሠረት በማድረግ  የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥቅምት 7 ቀን 2004 ዓ.ም ባካሔደው የሁለተኛ ዓመት የሥራ ዘመን ሁለተኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ያለመከሰስ መብታቸው እንዲነሳ መወሰኑን ተከትሎ ነው፡፡

ከተጠርጣሪው የሙስና ወንጀል ምርመራ ጋር በተያያዘ ኮሚሽኑ ከ2003 ዓ.ም መጀመሪያ ጀምሮ ባደረገው ክትትልና ማጣራት በፌዴራል መንግስት የበጀት ድጎማ እና በክልሉ በጀት በ1998 ዓ.ም የጣና በለስ የሴቶች አዳሪ ትምህርት ቤትን፣ የግልገል በለስ መምህራን ኮሌጅን እና የአሶሳ ሙያና ቴክኒክ ማሰልጠኛ ተቋምን ለማስገንባት በተደረገው እንቅስቃሴ የጨረታውን ሒደት እንዳዛባ መረጃዎች ጠቁመዋል፡፡

በዚህም መሠረት የክልሉ የትምህርት ቢሮ ኃላፊ ከነበሩት ከአቶ ሀብታሙ ሂካ እና ከጥቂት ኮንትራክተሮች ጋር በመመሳጠር በመንግሥት የግዥ መመሪያ መሠረት ግልፅ ጨረታ በማውጣት፣ አቅሙ ያላቸው ተወዳዳሪዎችን በመጋበዝና በጥራት ማሰራት ሲገባቸው በውስን ጨረታ እንዲፈፀም ትዕዛዝ በመስጠት በመንግሥት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዲደርስ በማድረግ ተጠርጥረዋል፡፡

በሌላ በኩል የእነዚህ ፕሮጀክቶች ስራ ውል ከተገባበት ከ1998 ዓ.ም መጨረሻ እና ከ1999 ዓ.ም መጀመሪያ ጀምሮ በ13 ወራት ውስጥ ተሰርቶ እንዲጠናቀቅ ውል የተገባ ቢሆንም ከተቋራጮቹ ጋር አስቀድሞ በተፈጠረ ሕገ-ወጥ የጥቅም ግንኙነት ምክንያት ፕሮጀክቶቹ እስካሁን ካለመጠናቀቃቸውም በላይ ለተቋራጮቹ ከውሉ ውጭ ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ እንዲከፈል ምክንያት መሆናቸው ታውቋል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ አቶ ያረጋል የመንግሥት ተቀጣሪ ሆኖ ሳለ በሕጋዊ መንገድ ሲያገኙት ከነበረው ገቢ በላይ ሀብት ያፈሩ ለመሆኑ አመላካች ማስረጃዎች መገኘታቸውንም ኮሚሽኑ ባካሄደው ማጣራት ተደርሶበታል፡፡

በመሆኑም አቶ ያረጋል አይሸሹም ከተጠረጠሩበት የሙስና ወንጀል ጋር በተያያዘ ጥቅምት 9 ቀን 2004 ዓ.ም በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን፣ ቀደም ሲል በቁጥጥር ስር የዋሉት የክልሉ የትምህርት ቢሮ ኃላፊ የነበሩት አቶ ሀብታሙ ሂካ እና በአባሪነት የተጠረጠሩ የሥራ ተቋራጮችም ጉዳይ በምርመራ ላይ ይገኛል፡፡

   
 

በከባድ የእምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል የተከሰሰ ግለሰብ በጽኑ እስራት እና በገንዘብ እንዲቀጣ ተወሰነበት

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በከባድ የእምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል ክስ የመሰረተበት ግለሰብ በ5 ዓመት ፅኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ጥቅምት 13 ቀን 2004 ዓ.ም በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

ተከሳሽ ስለሺ ንጉሴ በአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለሥልጣን አዲስ ከተማ ቅርንጫፍ ውስጥ የንብረት አስተዳደር ኦፊሰር ሆኖ ሲሰራ ተገቢ ያልሆነ ብልጽግና ለማግኘት በማሰብ  የቅርንጫፉን ግምጃ ቤት ከተረከበበት ከሀምሌ ወር 2001 ዓ.ም እስከ የካቲት ወር 2002 ዓ.ም በነበረው ጊዜ ግምታቸው ብር 147,116 (አንድ መቶ አርባ ሰባት ሺ አንድ መቶ አስራ ስድስት ብር) የሆኑ የውሃ ቆጣሪዎችን እና ጌት ቫልቮችን ጨምሮ በኦዲት ሪፖርቱ ላይ በጉድለት የተዘረዘሩትን የተለያዩ 36 ዓይነት የመንግስት ንብረቶችን በማጉደሉ በከባድ የእምነት ማጉደል ክስ እንደተመሰረተበት የኮሚሽኑ የክስ መዝገብ አመልክቷል፡፡

በመሆኑም ተከሳሹ በኮሚሽኑ የቀረበበትን የሰነድና የሰው ማስረጃ መከላከል ባለመቻሉ በ5 ዓመት ጽኑ እስራት እና በብር 3000 (ሶስት ሺህ ብር) እንዲቀጣ ተወስኖበታል፡፡

   
 

መንግሥታዊ ሰነዶችን አስመስሎ በማዘጋጀት የሙስና ወንጀል የተከሰሰ ግለሰብ ተፈረደበት

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን መንግሥታዊ ሰነዶችን አስመስሎ በማዘጋጀትና ወደ ሐሰት መለወጥ የሙስና ወንጀል ክስ የመሰረተበት ግለሰብ በ4 ዓመት ከ4 ወር ፅኑ እስራት እንዲቀጣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት ጥቅምት 14 ቀን 2004 ዓ.ም. በዋለው ችሎት ውሳኔ አስተላለፈ፡፡

ተከሳሽ ጌታቸው ትርኩ በአዲስ አበባ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት ውስጥ የመዝገብ ቤት ሠራተኛ ሆኖ ይሰራ በነበረበት ወቅት የመንግሥትን ጥቅም በመጉዳት ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለራሱ እና ለሌሎች ሰዎችም ለማስገኘት በማሰብ በተጠርጣሪዎች ላይ በዋስትና የተያዘ ገንዘብ እና ንብረት በዳኞች ትዕዛዝ ሳይሰጥ ትዕዛዝ እንደተሰጠ በማስመሰል የዳኞችን ስም፣ የእጅ ጽሁፍ፣ ፊርማና የስም ቲተር በሐሰት በመጠቀም እንዲሁም በምድብ ችሎቱ የሚሰሩ የፍርድ ኦፊሰሮችን አሳስቶ በማስፈረም በ2001 እና በ2002 ዓ.ም በተለያዩ ወራትና ቀናት የሙስና ወንጀል መፈጸሙን የክስ መዝገቡ ያመለክታል፡፡

በአጠቃላይ ተከሳሹ በተጠርጣሪዎች ስም የተያዘ የዋስትና ገንዘብና ንብረት በሕገወጥ መንገድ ለማስለቀቅ እና ወጪ ለማድረግ በማሰብ በምድብ ችሎቱ ዳኞች የተሰጠ ትዕዛዝ በሌለበት ሁኔታ ትዕዛዝ በዳኞች እንደተሰጠ በማስመሰል የተለያዩ ሐሰተኛ ትዕዛዞችን በማዘጋጀቱ በፈፀመው መንግሥታዊ ሰነዶችን አስመስሎ በማዘጋጀትና ወደ ሐሰት መለወጥ የሙስና ወንጀል ክስ ተመስርቶበታል፡፡

በመሆኑም ተከሳሹ የቀረበበትን የሰውና የሰነድ ማስረጃ መከላከል ባለመቻሉ በ4 ዓመት ከ4 ወር ፅኑ እስራት እንዲቀጣ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

   
 

የኮሚሽኑን ስትራቴጅያዊ ዕቅድ ወደ ግለሰብ ፈፃሚዎች የማውረድ ሥራ (Cascading) ተጀመረ

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽንን የውጤት ተኮር ሥርዓት ግንባታ ዕቅድ ከኮሚሽኑ ወደ ሥራ ሒደቶች፣ ከሥራ ሒደቶች ደግሞ ወደ ቡድኖች ለማውረድ ርክክብ መካሄዱን ተከትሎ ስትራቴጅክ ዕቅዱ ላይ የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት እንዲያግዝ ዕቅዱ ወደ ዋና ዋና ተግባራት ተመንዝሮ ለፈፃሚ ባለሙያዎች እንዲወርድ እየተደረገ እንደሚገኝ ከኮሚሽኑ የጥናትና ለውጥ ሥራ አመራር ዳይሬክቶሬት የተገኘ መረጃ አመለከተ፡፡

ዕቅዱ ወደ ዋና ዋና ተግባራት ተለውጠው በየቡድኖቹ ለሚገኙ ፈጻሚ ባለሙያዎች እንዲወርዱ ሲደረግም ዋና ተግባራቱን ከጊዜ፣ ከጥራትና ከመጠን አኳያ ለመለካት በሚያስችል መልኩ ተቃኝተው እንደሆነም ለመረዳት ተችሏል፡፡

በመሆኑም እያንዳንዱ ዋና ተግባር ከዚህ በላይ ከተጠቀሱት ሦስት መለኪያዎች በሁሉም ወይም በሁለቱ ያለበለዚያም በአንዱ ሊለካ በሚችል መልክ እየተቀረፀ እንደሚገኝ ታውቋል፡፤

እነዚህ የተቀመጡ መለኪያዎች ሶስት የአፈፃፀም ደረጃዎች የሚኖራቸው ሲሆን ደረጃዎቹም "አረንጓዴ"፣ "ቢጫ" እና "ቀይ" በሚል ተለይተው የሚቀመጡ ናቸው፡፡ በዚህ መሠረት አረንጓዴው በጣም ከፍተኛና ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብን፣ ቢጫው አማካኝ ውጤት ማምጣትን፣ ቀዩ ደግሞ ዝቅተኛ ውጤት ማግኘትን እንደሚያመለክትም ከዳይሬክቶሬቱ ከተገኘው መረጃ ለመገንዘብ ተችሏል፡፡

በመዘጋጀት ላይ ያሉት እነዚህ ዋና ዋና ተግባራት በየቡድኖቹ ለሚገኙ ፈፃሚ ባለሙያዎች የሥራ ደረጃቸውን ባገናዘበ መልኩ ተቆጥሮ የሚሰጣቸው ሲሆን እያንዳንዱ ፈጻሚ ባለሙያም የተሰጠውን ሥራ ለማከናወን ከቡድን አስተባባሪው ጋር ቻርተር የሚፈራረም መሆኑንም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ዋና ዋና ተግባራቱን ለፈጻሚ ባለሙያዎች የማውረድ ሥራ የተጀመረው መስከረም 18 ቀን 2004 ዓ.ም ሲሆን ይህም ስራ እስከ መስከረም 30 ቀን 2003 ዓ.ም እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል፡፡

   

 

ኮሚሽኑና የዓለም ባንክ የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረሙ

በዓለም ባንክ ድጋፍ በኢትዮጵያ ውስጥ ተግባራዊ በሚሆኑ ፕሮጀክቶች ላይ ሙስናና ብልሹ አሠራር እንዳይፈፀም ለመከላከልና ወንጀሉ ተፈጽሞ ቢገኝ እንኳን መረጃ በመለዋወጥ አጥፊዎቹ ለሕግ የሚቀርቡበትን ሁኔታ ተግባራዊ ለማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽንና የዓለም ባንክ የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረሙ፡፡

የመግባቢያ ሰነዱን በኮሚሽኑ ዋና መስሪያ ቤት መስከረም 23 ቀን 2004 ዓ.ም የተፈራረሙት ኮሚሽኑን በመወከል የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን ሲሆኑ፣ በዓለም ባንክ በኩል ደግሞ በተወካያቸው በኩል የዓለም ባንክ የኢንቴግሪቲ ምክትል ፕሬዚዳንት ሚስተር ሌዎናርድ ኤፍ. ማካርቲ ናቸው፡፡

ሁለቱ ተቋማት ባደረጉት ስምምነት መሠረት የመግባቢያ ሰነዱ በአገራችን ውስጥ በዓለም ባንክ የገንዘብ ድጋፍ በሚካሄዱ ፕሮጀክቶች ላይ የሚፈጸሙ የሙስና ወንጀሎችንና ብልሹ አሠራሮችን ለመከላከልና እንዲሁም ችግሮቹ ከተከሰቱ በኋላ ወንጀሉን በመመርመር ለሕግ ለማቅረብ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ አስፈላጊ መረጃዎችን lመለዋወጥ ይቻላቸዋል፡፡

አሁን በተደረሰው ስምምነት መሠረት ከእነዚህ ፕሮጀክቶች ጋር በተያያዘ በሚፈፀም ሙስናና ብልሹ አሰራር ሳቢያ በኮሚሽኑም ሆነ በዓለም ባንክ ተነሳሽነት በሚካሄድ የሙስና መከላከል የምርመራና እንዲሁም የመረጃ ማሰባሰብ ሥራ ላይ ሁለቱ አካላት ተደጋግፈው የሚሰሩ ይሆናል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ኮሚሽኑና የዓለም ባንክ የጋራ ፍላጎቶቻቸው በሆኑ ጉዳዮች ላይ የተጣሉባቸውን ኃላፊነቶች ለመወጣት በሚያደርጉት ጥረት ተባብረው ለመስራት ስምምነት ላይ የደረሱ ሲሆን፣ በሁለቱ ተቋማት የሥልጣን ክልል ስር በሆኑ ጉዳዮች ዙሪያ የምርመራ ሥራ በሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ አንደኛው አካል ለሌላው መረጃ ለመስጠትና የመፍትሔ ሐሳብ ለማቅረብ ይችላል፡፡

በሌላ በኩል በዓለም ባንክ የፋይናንስ ድጋፍ አማካኝነት በአገራችን በትምህርት፣ በኮንስትራክሽን፣ በጤና፣ በቴሌኮም፣ በማዕድን፣ በውሃ፣ በመሬት አስተዳደር እና በፍትህ ዘርፍ ባለፉት ዓመታት የዓለም ባንክ በአገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ ባካሄደው ዲያግኖስቲክ ጥናት (Diagnostic Study) ላይ ኮሚሽኑ አስፈላጊውን ትብብር ማድረጉ የሚታወስ ሲሆን፣ የጥናቱ ውጤትም ታትሞ በቅርቡ ለሕዝብ ይፋ እንደሚደረግ ለመረዳት ተችሏል፡፡

በተመሳሳይም የዓለም ባንክ ቀደም ሲል ቦትስዋና እና ዋሽንግተን ላይ “Corruption Hunters Network” በሚል ስያሜ ባዘጋጀው አውደ-ጥናት አገሮች ከዓለም ባንክ ጋር ተባብረው እንዲሰሩ ስምምነት ላይ የተደረሰ ሲሆን፣ አሁን ሁለቱ ተቋማት የተፈራረሙት የመግባቢያ ሰነድም ይህን ስምምነት መሠረት በማድረግ እንደሆነ ለመረዳት ተችሏል፡፡

ይህ ተግባራዊ እርምጃም የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽንን ስምምነቱን በቅድሚያ ተግባራዊ ማድረግ የቻለ ተቋም ያደረገው ሲሆን፣ የአሁኑ የመግባቢያ ሰነድ በሁለቱ አካላት መፈረምም ቅንጅታዊ አሠራሩን የበለጠ ቅርጽ ለማስያዝና የሁለቱን አካላት የጋራ ጥረት ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚያስችል ለመገንዘብ ተችሏል፡፡

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በኢትዮጵያ ውስጥ በዓለም ባንክ የሚካሄዱ ፕሮጀክቶችን ከሙስናና ከብልሹ አሠራር ለመታደግ የሚያደርገውን ጥረት አስመልክቶም የዓለም ባንክ ከፍተኛ አድናቆት እንዳለውና ይህም ጥረት በዘንድሮው የባንኩ ዓመታዊ ሪፖርት ተገቢ ስፍራ እንደሚሰጠው ባንኩ እ.ኤ.አ ሴፕቴምበር 20 ቀን 2011 ዓ.ም ለኮሚሽኑ በጻፈው የምስጋና ደብዳቤ ገልጿል፡፡

   
 

የኡጋንዳ ሪፑብሊክ የመንግስት ኢንስፔክተር ጄኔራል ስለኮሚሽኑ አደረጃጀትና አሠራር መግለጫ ተሰጣቸው

የኡጋንዳ ሪፐብሊክ ኢንስፔክተር ጄኔራል ሚስተር ባኩ ራፋኤል ኦቡድራ ስለፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን አደረጃጀትና የሥራ እንቅስቃሴ በኮሚሽኑ የሥራ ኃላፊዎች መስከረም 2 ቀን 2004 ዓ.ም ማብራሪያ ተሰጣቸው፡፡  

በኮሚሽኑ ኮሚሽነር በክቡር አቶ አሊ ሱለይማን እና በየዳይሬክተሬቶቹ ኃላፊዎች ለእንግዳው በኮሚሽኑ የማኔጅመንት የስብሰባ አዳራሽ ሰፊ ማብራሪያ የቀረበላቸው ኮሚሽኑ የሥነምግባር ትምህርትን በማስፋፋት፣ ሙስናን በመከላከል፣ በሙስና ወንጀል ምርመራና ክስ አመሰራረት እንዲሁም በሀብት ምዝገባ እንቅስቃሴዎች ዙሪያ ኮሚሽኑ እስከአሁን ያከናወናቸውን ተግባራት አስመልክቶ  ነው፡፡

ሚስተር ባኩ ራፋኤል ኦቡድራ ኮሚሽኑ ስለሚያካሂደው የምርመራና ክስ አሠራር በተደረገላቸው ማብራሪያ የኮሚሽኑ የሕግ ባለሙያዎች የቢሮ እና የችሎት ዐቃቤ ሕጎች በሚል የተለየ አደረጃጀት እንዲኖራቸው መደረጉ እንዲሁም በከፍተኛ ፍርድ ቤት የሙስና ወንጀልን ብቻ የሚያዩ ሶስት ችሎቶች የተደራጁ መሆናቸው ለአገራቸው እንደ አዲስ ተሞክሮ ሊወሰድ የሚችል አሠራር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ኢንስፔክተር ጄኔራሉ በበኩላቸው በፀረ-ሙስና እና በእንባ ጥበቃ (Ombudsman) እንዲሁም በሀብት ማሳወቅና ምዝገባ ዙሪያ የኡጋንዳ ሪፐብሊክን ተሞክሮ ለኮሚሽኑ የሥራ ኃላፊዎች አካፍለዋል፡፡

ሚስተር ባኩ ራፋኤል ኦቡድራ በበላይነት የሚመሩት የመንግስት ኢንስፔክቶሬት ጄኔራል በኡጋንዳ ሪፑብሊክ የፀረ-ሙስናን፣ የእንባ ጥበቃንና የሀብት ምዝገባ ሥራዎችን የሚከታተል ሲሆን ተቋሙ በተለይ በሀብት ምዝገባና የምዝገባውን ትክክለኛነት በማረጋገጥ ረገድ ያለውን ተሞክሮ ለኮሚሽኑ ለማካፈል ዝግጁ መሆኑን ገልፀዋል፡፡

   
 

የዴሞክራቲክ ተቋማት የትብብርና የምክክር የጋራ መድረክ 2ኛ መደበኛ ስብሰባ ተካሄደ

በፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን፣ በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እና በኢ.ፌ.ዴ.ሪ. የሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም አማካኝነት የተመሰረተው የዴሞክራቲክ ተቋማት የትብብርና የምክክር የጋራ መድረክ 2ኛ መደበኛ ስብሰባ ጳጉሜ 3 ቀን 2003 ዓ.ም በሐርመኒ ሆቴል ተካሔደ፡፡

የምክክር የጋራ መድረኩ ባካሄደው ስብሰባ የሙስና ወንጀል ድንጋጌዎችን ለማሻሻል በቀረበ ረቂቅ አዋጅ፣ የተሻሻለውን የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅን እንደገና ለማሻሻል በቀረበ ረቂቅ አዋጅ እንዲሁም የተሻሻለውን የፀረ-ሙስና ልዩ የሥነስርዓትና የማስረጃ ሕግ አዋጅን እንደገና ለማሻሻል በቀረበ ረቂቅ አዋጅ ላይ በመወያየት ግልጽነት በሚጎድላቸው፣ አሻሚ በሆኑ እና ማሻሻያ በሚያስፈልጋቸው ነጥቦች ላይ ማስተካከያ ለማድረግ የሚረዱ አስተያየቶች ቀርበዋል፡፡  

በውይይቱ ወቅት የሙስና ወንጀል ድንጋጌዎችን እንደገና ለማሻሻል የተፈለገው የሙስና ወንጀል ድንጋጌዎች በግል ዘርፉ የሚፈፀሙ ተመሳሳይ ወንጀሎችን ያላካተቱ በመሆናቸውና በመንግስት ዘርፍም መካተት የነበረባቸው ነገር ግን ያልተካተቱ የሙስና ተግባራት በመኖራቸው እንደሆነ ተገልጿል፡፡  

በመንግሥት ተቋማትና ሰራተኞች ዙሪያ የሚያተኩሩ አንዳንድ ድንጋጌዎች ግልፅነት የሚጎድላቸውና ለአፈፃፀም አስቸጋሪ መሆናቸው በጥናት መረጋገጡ በአዋጁ ማሻሻል አስፈላጊነት ላይ በምክንያትነት ቀርቧል፡፡

የተሻሻለውን የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ማቋቋሚያ አዋጅን እና የተሻሻለው የፀረ-ሙስና ልዩ የሥነሥርዓትና የማስረጃ ሕግ አዋጅን እንደገና ለማሻሻል ያስፈለገውም በቅደም-ተከተል አዋጅ ቁጥር 433/1997 እና 434/1997 በስራ ላይ በቆዩባቸው ዓመታት አንዳንድ ድንጋጌዎቻቸው ግልፅነት ስለሚጎድላቸውና ለፀረ-ሙስና ትግሉ ውጤታማነት የሚረዱ በአዋጆቹ መካተት የነበረባቸው ግን ያልተካተቱ ጉዳዮች መኖራቸው ግንዛቤ በማግኘቱ መሆኑም ተጠቅሷል፡፡

በስብሰባው ላይ ከሶስቱ የዲሞክራሲያዊ ተቋማት ከተውጣጡ የሥራ ኃላፊዎች በተጨማሪ ከተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) የተወከሉ ሁለት ባለሙያዎችም መገኘታቸው ታውቋል፡፡  

በስብሰባው ማጠቃለያ ላይ በ2004 በጀት ዓመት በጋራ መድረኩ የሚካሔዱ ስብሰባዎችን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን እንዲስተናግድ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ 

   
 

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ሀብታቸውን አስመዘገቡ

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ሀብታቸውን እንዲያሳውቁ እንዲያስመዘግቡ የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን መስከረም 19 ቀን 2003 ዓ.ም በከተማ አስዳደሩ ስብሰባ አዳራሽ ባዘጋጀው ዝግጅት ከ200 በላይ የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ተሚዎች ሀብታቸውን አስመዘገቡ፡፡

ሀብታቸውን ካስመዘገቡት መካከል የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ፣ ም/ከንቲባ፣ ዋና አፈ ጉባዔ፣ ም/አፈ ጉባዔ፣ የከተማ ነክ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት፣ የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት፣ የቢሮ ኃላፊዎች እንዲሁም በቀበሌ ደረጃ የሚገኙ አመራሮች ይገኙበታል፡፡  

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ክቡር አቶ አሰድ ዚያድ በሥነሥርዓቱ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር በአንድ አገር ግልፅነትንና ተጠያቂነትን ለማስፈን የሀብት ምዝገባ የሚኖረውን አስተዋጽኦ ጠቅሰው፣ የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ተሿሚዎችም ለሀብት ምዝገባው ተግባራዊነት ያላቸውን ዝግጁነት ገለጸዋል፡፡

የክቡር ከንቲባውን ንግግር ተከትሎ የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር በከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የሚከናወን ሀብት የማሳወቅና የማስመዝገብ የሥራ ስኬት በከተማ አስተዳደሩ ስር ለሚገኙ ሌሎች ተቋማትም በቂ ተሞክሮ ተደርጎ ሊወሰድ ስለሚችል የከተማ አስተዳደሩ ለአዋጁ ተፈጻሚነት ለሚያደርገው ጥረት ኮሚሽኑ ልዩ ትኩረት እንደሚሰጥ አስገንዝበዋል፡፡

በዋዜማው በከተማ አስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ ስር የተደራጁ ወጣቶች በከተማው ዋና ዋና መንገዶች ላይ የማርሽ ባንድ ትርኢት በማሳየት፣ በዕለቱ ደግሞ የሀብት ማሳወቅና ማስመዝገብ ጠቀሜታን የተመለከተ መዝሙር በማቅረብ ለዝግጅቱ ልዩ ድምቀት ያጎናፀፉት መሆኑም ታውቋል፡፡

   
 

የኮሚሽኑ ሠራተኞች የሰንደቅ ዓላማ ቀንን አከበሩ

በብሔራዊ ደረጃ ለ4ኛ ጊዜ መስከረም 15 ቀን 2004 ዓ.ም የተከበረውን ብሔራዊ የሰንደቅ ዓላማ ቀን የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሠራተኞች ባንዲራ በመስቀል ሥነሥነርዓት እና ቀኑን አስመልክቶ በተዘጋጀ የውይይት መድረክ ላይ በመሳተፍ አከበሩ፡፡

“ሰንደቅ ዓላማችንና የህዳሴው ግድብ ብሔራዊ ኩራታችን ናቸው” በሚል መሪ ቃል ዕለቱ በአገር አቀፍ ደረጃ የተከበረ ሲሆን የኮሚሽኑ ሠራተኞችም በኮሚሽኑ ቅጥር ግቢ ውስጥ ሰንደቅ ዓላማ የማውጣት ሥነሥርዓት ሲካሔድ የኢትዮጵያ ህዝብ ብሔራዊ መዝሙር በመዘመር ለብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ ያላቸውን ክብር ገልፀዋል፡፡

ከብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ የማውጣት ሥነሥርዓት በኋላ የኮሚሽኑን ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማንን በመወከል የኮሚሽኑ የሥነምግባር ትምህርትና ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳሬክተር አቶ ብርሐኑ አሰፋ ባደረጉት ንግግር ሰንደቅ ዓላማችን የአንድነታችን፣ የነፃነታችን እና የኩራታችን መገለጫ መሆኑን ገልፀው የዘንድሮው የሰንደቅ ዓላማ ቀን የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱን ተግባራዊ ማድረግ በጀመርንበትና በተለይም ደግሞ በህዳሴው ግድብ ግንባታ ላይ ርብርብ በምናደርግበት ጊዜ የሚከበር በመሆኑ ቀኑን ስናከብር አገራችንን ከድህነትና ከኋላ ቀርነት የማላቀቁን ጉዳይ ለአፍታም ሳንዘነጋ መሆን እንዳለበት አስረድተዋል፡፡  

የሰንደቅ ዓላማ የማውጣት ሥነስርዓቱን ተከትሎም የኮሚሽኑ ሠራተኞች “ብሔራዊ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ታሪካዊ አመጣጥ” እና “የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ሰንደቅ ዓላማ ሕጋዊ ማዕቀፎች” የሚሉ ጽሑፎችን መሠረት በማድረግ በተዘጋጀ የውይይት መድረክ ላይ ተሳትፈዋል፡፡

በመጨረሻም የኮሚሽኑ ሠራተኞች የ2004 ዓ.ም የሰንደቅ ዓላማ ቀን ቃለ-መሀላ ፈጽመዋል፡፡ ቃለ-መሀላውም “እኛ ኢትዮጵያውያን የድህነትና የኋላ ቀርነት ዘመን ከሀገራችን ተወግዶ፤ ኢትዮጵያችን በልማትና በዴሞክራሲ ጎዳና በፍጥነት ተራምዳ፣ በአስር ዓመት ጊዜ ውስጥ መካከለኛ ገቢ ካላቸው የዓለም ሕዝቦች ተርታ ትሰለፍ ዘንድ፣ የተነደፈውን የአምስት ዓመት የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድ እና ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታን ከመንግስታችን ጎን ተሰልፈን ተግባራዊ በማድረግ የኢትዮጵያ ህዳሴ የማይቀለበስበት ደረጃ ላይ ለማድረስ በሀገራችን ሰንደቅ ዓላማ ፊት ቃል እንገባለን!” የሚል ሲሆን ከዚህ በኋላ የበዓሉ አከባበር ፍጻሜ ሆኗል፡፡

   
 

ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ አማካሪ መሐንዲሶችና አርክቴክቶች ማህበር ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረመ

የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እና የኢትዮጵያ አማካሪ መሐንዲሶችና አርክቴክቶች ማህበር ሙስናንና ብልሹ አሰራርን በኮንስትራክሽን ዘርፍ ለመከላከል በጥናትና በአቅም ግንባታ ዘርፍ ተባብረው ሊሰሩ የሚችሉበትን የመግባቢያ ሰነድ መስከረም 12 ቀን 2004 ዓም ተፈራረሙ፡፡

የመግባቢያ ሰነዱን በኮሚሽኑ የማኔጅመንት ስብሰባ አዳራሽ የተፈራረሙት የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽንን በመወከል ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን ሲሆኑ፣ የኢትዮጵያ አማካሪ መሀንዲሶችና አርክቴክቶች ማህበርን በመወከል ደግሞ የማህበሩ ፕሬዚዳንት የሆኑት አቶ እሸቴ ሙላት ናቸው፡፡

ሁለቱ አካላት በተፈራረሙት የመግባቢያ ሰነድ መሠረት በኮንስትራክሽን ዘርፍ ብልሹ አሠራርንና ሙስናን ለመከላከል እንዲቻል በአሠራር ሥርዓት ጥናት፣ በአውደ-ጥናት፣ በሥልጠና፣ በተፅዕኖ ግምገማ ጥናት እንዲሁም በዘርፉ የምርጥ ተሞክሮ ቅመራ ዙሪያ ተባብረው ይሰራሉ፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ኮሚሽኑና ማህበሩ በኮንስትራክሽን ዘርፍ የሚታየውን ብልሹ አሠራርና ሙስና ለመከላከል የሚረዱ ተስማሚ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዘዴዎች በመምረጥ ሥራ ላይ ለማዋል፣ የሥነምግባር ትምህርትን ለማህበሩ አባላት ለማዳረስ እንዲሁም በዘርፉ ለሙስና ተጋላጭ የሆኑ አሰራሮችን በመለየት የሙስና መከላከል ሥራ ለማከናወን በጋራ የሚሰሩ ይሆናል፡፡

በመግባቢያ ሰነዱ ላይ የተመለከቱትን የትብብር መስኮች ተፈጻሚ ለማድረግም ሁለቱ አካላት ባለሙያዎችን በማቀናጀት እና መረጃን በመለዋወጥ በዘርፉ የሚስተዋለውን የሙስና ችግር ለመከላከል የሚያስችሉ እርምጃዎች በጋራ የሚወሰዱበትን መንገድ ተግባራዊ ለማድረግ ተባብረው ይሰራሉ፡፡ በተመሳሳይም በኮንስትራክሽን ዘርፍ ለተሰማሩ አማካሪ መሐንዲሶች፣ ተቋራጮች እና ሌሎች ባለሙያዎች የሚያገለግል የሥነምግባር ደንብ የሚዘጋጅበትን ሁኔታ ተፈጻሚ ለማድረግም በቅንጅት የሚንቀሳቀሱ ይሆናል፡፡

ከመግባቢያ ሰነዱ የፊርማ ሥነሥርዓት በኋላ የፌዴራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን ባደረጉት ንግግር ኮሚሽኑ ሙስናን እና ብልሹ አሰራርን በመዋጋት ረገድ በአስተባባሪነትና ማዕከላዊ አካል ሆኖ ከማገልገል ባሻገር ሙስናን በወሳኝነት የመዋጋት ድርሻ የሕዝብ መሆኑን ገልፀው፣ የኢትዮጵያ አማካሪ መሐንዲሶችና አርክቴክቶች ማህበርም በስምምነቱ ማዕቀፍ ውስጥ ከኮሚሽኑ ጋር ተባብሮ ለመስራት ዝግጁ መሆኑ እንዲሚያስመሰግነው ገልጸዋል፡፡

በተመሳሳይም የኢትዮጵያ አማካሪ መሃንዲሶችና አርክቴክቶች ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ እሸቴ ሙላት በበኩላቸው ማህበሩ ከኮሚሽኑ ጋር የተፈራረመው የመግባቢያ ሰነድ ለማህበሩ አባላት ትምህርትና ሥልጠና ለመስጠት እንዲሁም እያንዳንዱን ሙያተኛ በቅርብ ለመከታተል የሚያስችለው በመሆኑ አማካሪ መሐንዲሶች ከብ