|
በሥነምግባር እና ሥነዜጋ ክበባት እንቅስቃሴ ላይ የተዘጋጀ የልምድ መለዋወጫ መድረክ በመካሄድ ላይ ነው የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከየክልል ትምህርት ቢሮዎች ለተውጣጡ የተጓዳኝ ትምህርት ኤክስፖርቶችና የሥነምግባርና ሥነዜጋ ትምህርት ዩኒት ኃላፊዎች እንዲሁም ለመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሥነምግባር እና ሥነዜጋ ክበባት መሪዎች እና ርዕሰ መምህራን ያዘጋጀውና በሥነምግባርና ሥነዜጋ ክበባት እንቅስቃሴ ዙሪያ የሚካሄደው የሁለት ቀናት የልምድ መለዋወጫ መድረክ ተጀመረ፡፡ የመድረኩ ዓላማ ለተሣታፊዎች የሥነምግባር እና የሙስና ፅንሰ ሀሳብን ለማሳወቅ እና በየክልሉ በሚገኙ ትምህርት ቤቶች የተቋቋሙ የሥነምግባርና ሥነዜጋ ክበባት እንቅስቃሴ ያለበትን ደረጃ ለመገምገም እንዲሁም በክበባት እንቅስቃሴ ዙሪያ ልምድ ለመለዋወጥ ነው፡፡ በኮሚሽኑ የስብሰባ አዳራሽ ታህሳስ 2ዐ ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም በተጀመረው በዚህ የልምድ መለዋወጫ መድረክ ላይ የየትምህርት ቤቶች የሥነምግባር እና ሥነዜጋ ክበባት እንቅስቃሴዎች የተሞክሮ የልምድ ልውውጥ እንደሚደረግም ታውቋል፡፡ የአዲስ አበባ እና የድሬድዋ ከተማ መስተዳድሮችን ጨምሮ ከሁሉም ክልሎች የተውጣጡ 9ዐ ያህል የትምህርት ባለሙያዎች በሚሳተፉበት በዚህ መድረክ ላይ የክበባትን እንቅስቃሴ ለመደገፍና ለማጠናከር በኮሚሽኑ በኩል እየተከናወኑ ያሉ ተግባሮች የሚቀርቡ ሲሆን በ2ዐዐ1 ዓ.ም ክበባት በሚያከናውኗቸው ሥራዎች ላይም ውይይት ይካሄዳል፡፡ |
|
በሙስና ወንጀል የተጠረጠሩ በቁጥጥር ስር ዋሉ በፌደራል ትራንስፖርት ባለሥልጣን በተለያየ የሥራ ኃላፊነት ላይ ተሰማርተው ሲያገለግሉ የነበሩ ሠራተኞችና ቤተልሄም ልሳኑ የተባለ ማተሚያ ቤት ሥራ እስኪያጅ እና ደላሎች በአጠቃላይ ስድስት ሰዎች ሀሰተኛ የመንጃ ፈቃዶችን በማዘጋጀት ለተለያዩ ግለሰቦች በመስጠት ሕገ ወጥ ድርጊት በመጠርጠራቸው በፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በቁጥጥር ስር ዋሉ፡፡ ኮሚሽኑ በወንጀሉ ድርጊት ተባባሪ እንደሆነ በተጠረጠረው ማተሚያ ቤት ላይ ባደረገው ፍተሻ ለሕገወጥ አገልግሎት የተዘጋጁ ከ5ዐ በላይ የመንግሥት እና የግል ተቋማት ማሕተሞች እና ቲተሮች እንዲሁም የተለያዩ ሐሰተኛ ሰነዶች በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ በሕገወጥ ተግባር ላይ ተሰማርቶ በቆየው ማተሚያ ቤት ላይ በተደረገ ፍተሻ በሀሰተኛ መንገድ ተዘጋጅተው በቁጥጥር ስር ከዋሉት ማሕተሞችና ቲተሮች መካከል በመንግሥት እና በግል የከፍተኛ ትምሕርት ተቋማት፣ በሐይማኖት ተቋማት፣ በመኖሪያ ቤት ሕብረት ሥራ ማሕበራት፣ በግል ድርጅቶች እንዲሁም በተለያዩ የክልል መንግስታት መ/ቤቶች ስም የተቀረፁ ይገኙበታል፡፡ በተመሳሳይም በሀሰተኛ መንገድ ተዘጋጅተው በቁጥጥር ስር ከዋሉት ሰነዶች መካከል የሕክምና የዶክተሬት ዲግሪን ጨምሮ የመንግሥት እና የግል ከፍተኛ የትምሕርት ተቋማት የትምህርት ማስረጃዎች፣ የንግድ ፈቃዶች እና እስከ አምስተኛ ደረጃ የመንጃ ፈቃድ ደብተሮች ይገኙባቸዋል፡፡ በሙስና ወንጀሉ ላይ እንደተሳተፉ የተጠረጠሩት አራት የፌደራል ትራንስፖርት ባለሥልጣን ሠራተኞች ሀሰተኛ የመንጃ ፈቃድ ፈላጊ ግለሰቦችን በደላሎች አማካኝነት በማግኘት እና ለዚሁ ሕገወጥ ሥራቸው አስፈላጊ የሆኑ የተለያዩ ክልሎች የመንጃ ፈቃድ ደብተሮች እና ማሕተሞች ከሚያቀርብላቸው ከዚህ ማተሚያ ቤት ጋር ትስስር በመፍጠር ወንጀሉን ሲፈፅሙ እንደቆዩም ታውቋል፡፡ እነዚህ የባለሥልጣኑ ሠራተኞች በተለያዩ ክልሎች የመንገድ ትራንስፖርት ቢሮዎች የተሰጡ በሚመስል መንገድ በሀሰት የተዘጋጁ የመንጃ ፈቃዶች የፌደራል ትራንስፖርት ባለስልጣን በሚሰጣቸው የመንጃ ፈቃዶች እንዲቀየሩ ለማድረግ ሀሰተኛ ሰነድ ከሚያዘጋጁ ተባባሪዎቻቸው ጋር ሆነው ወንጀሉን ሲፈፅሙ ቆይተዋል፡፡ |
|
በኮሚሽኑ ድጋፍ ሲካሄድ የቆየው የብስክሌት ውድድር ተጠናቀቀ የዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀንን ምክንያት በማድረግ በፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የገንዘብ ድጋፍ ከታህሳስ 9 - 12 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም ሲካሄድ የቆየው አገር አቀፍ የብስክሌት ውድድር ተጠናቀቀ፡፡ የብስክሌት ስፖርትን ለማበረታታት እና የውድድሩን ሂደት ለሚከታተለው የሕብርተሰብ ክፍል አጋጣሚውን በመጠቀም የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ትምህርቶችን ለማስተላለፍ ኮሚሽኑ በያዘው ዓላማ መሠረት ‹‹ሙስናን በፅናት በመዋጋት መልካም አስተዳደርን እናረጋግጥ›› በሚል መሪ ሐሳብ በተካሄደው በዚህ ውድድር ላይ ከትግራይ፣ ከአማራ፣ ከደቡብ፣ ከኦሮሚያ እና ከሐረሪ ክልሎች እንዲሁም ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ ክለቦችና ምርጥ ብስክሌተኞች ተሳትፈዋል፡፡ የውድድሩን አሸናፊዎች ለመለየት በ6ዐ ብስክሌተኞች መካከል በጐዳና ላይ ከተካሄዱ ሁለት ውድድሮች በተጨማሪ ታህሳስ 12 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም መነሻውን በወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር ባደረገው 36 ዙር ውድድር ላይ በሽዎች የሚቆጠሩ የስፖርቱ ደጋፊዎች ተገኝተው ተወዳዳሪዎችን ሲያበረታቱ ውለዋል፡፡ በክለቦች መካከል በተካሄደው ውድድር ትራንስ ኢትዮጵያ፣ ጉና እና መሰቦ ሲሚንቶ በቅደም ተከተል ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ያለውን ደረጃ ሲይዙ ምርጥ ብስክሌተኞችን ካሰለፉ ክልሎች መካከል ደግሞ የድሬዳዋ፣ የደቡብ እና የአማራ ተወዳዳሪዎች በቅደም ተከተል ከ4ኛ እስከ 6ኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡ በዕለቱ አሸናፊ ለሆኑ የቡድን እና የግል ተወዳዳሪዎችም ከፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የሥነምግባር ትምሕርት እና ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዳይሬክተር ከአቶ ብርሃኑ አሰፋ የዋንጫ እና የሜዳሊያ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ ከኢትዮጵያ የብስክሌት ፌዴሬሽን ጋር በመተባበር ይህን ውድድር ለማዘጋጀት ኮሚሽኑ ብር 115,ዐዐዐ.ዐዐ የገንዘብ ድጋፍ እንዳደረገ ታውቋል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ4ኛ ጊዜ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ3ኛ ጊዜ ሕዳር 29 ቀን 2ዐዐዐ ዓ.ም የተከበረውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን አስመልክቶ የተካሔደውን የ2ዐዐዐ ዓ.ም አገር አቀፍ የወጣቶች የብስክሌት ውድድር ሻምፒዮና ኮሚሽኑ ብር 8ዐ,ዐዐዐ.ዐዐ ወጪ በማድረግ መደገፉ ይታወሳል፡፡ |
|
ለሥነምግባር መኮንኖች ሥልጠና እየተሰጠ ነው የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከተለያዩ የመንግሥት መ/ቤቶች እና የልማት ድርጅቶች ለተውጣጡ የሥነምግባር መኮንኖች ያዘጋጀው የስድስት ቀናት ሥልጠና እየተሰጠ ነው፡፡ ከታህሳስ 6-11 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም በኢምፔሪያል ሆቴል የሚካሄው እና 8ዐ የሥነምግባር መካንኖች የተሳተፉበት ሥልጠና በአሠራር ሥርዓት ጥናት፣ በሥነምግባር መከታተያ ክፍሎች ደንብ፣ በኮሚሽኑ የማቋቋሚያ አዋጅ፣ በሪፖርት አቀራረብ እና በሌሎችም ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው፡፡ የሥልጠናው ዓላማ የሥነምግባር መኮንኖቹ ወደየመስሪያ ቤቶቻቸው ሲመለሱ በሥልጠናው ያገኙትን ዕውቀት ለሥራ ባልደረቦቻቸው ለማካፈል እንዲችሉ እና በሥነምግባር እና በሙስና ዙሪያ በሕብረተሰቡ ውስጥ ጥያቄ ሊያስነሱ በሚችሉ ጉዳዮች ዙሪያ በቂ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችላቸውን አቅም ለማጐልበት ነው፡፡ |
|
ለሥነምግባር እና ሥነዜጋ መምሕራን የተዘጋጀ ሥልጠና ተሰጠ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በአዲስ አበባ ከተማ ዙሪያ ከሚገኙ 24 የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤቶች ለተውጣጡ 48 የሥነምግባር እና የሥነዜጋ መምሕራን ያዘጋጀው የመጀመሪያ ዙር ሥልጠና ተካሄደ፡፡ ከታህሳስ 6 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም ጀምሮ በኢምፔሪያል ሆቴል ለአምስት ቀናት የተካሄደው ሥልጠና ዓላማ ሠልጣኞቹ በሥነምግባር፣ በሙስና መከላከል፣ እንዲሁም በሙስና ወንጀሎችና በሚያስከትሉት ጉዳት ላይ በቂ ግንዛቤ ጨብጠው ከሙስና እና ከብልሹ አሠራር እንዲርቁ፣ ብሎም በሥነምግባር እና በሙስና ዙሪያ ለተማሪዎቻቸው በቂ ግንዛቤ ለማስጨበጥ የሚያስችላቸውን ዕውቀትና ክህሎት እንዲያገኙ ለማድረግ ነው፡፡ በተመሳሳይም ከታህሳስ 13 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ ከተማ ዙሪያ ከሚገኙና ሥልጠናውን ካልወሰዱ ሌሎች 25 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ለተውጣጡ 5ዐ የሥነምግባር እና ሥነዜጋ መምሕራን ተመሳሳይ ይዘት ያለው ሁለተኛ ዙር ሥልጠና ለአምስት ቀናት እንደሚሰጥ ለመረዳት ተችሏል፡፡ |
|
በሙስና ወንጀል የተከሰሰው በእስራት እንዲቀጣ ተወሰነ የአማራ ብሔራዊ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የባህርዳር ኤሌክትሪክ ኃይል ዲስትሪክት ቁጥር 1 አገልግሎት ኃላፊ የነበረው አዳነ አንዳርጌ ይማም በተከሰሰበት የሙስና ወንጀል ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ሕዳር 30 ቀን 2001 ዓ.ም በዋለው ችሎት በሁለት ዓመት ከስድስት ወር እስራት እንዲቀጣ ውሳኔ ሰጠ፡፡ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን በተከሳሹ ላይ የመሰረተው ክስ እንደሚያስረዳው ግለሰቡ መንግሥታዊ ሠነድን አስመስሎ የማዘጋጀትና በሥልጣን ያለአግባብ የመገልገል የሙስና ወንጀል ፈጽሟል፡፡ ተከሳሹ በመንግሥት የተጣለበትን ኃላፊነት ወደጐን በመተው የሥራ ባልደረባው የሆነችው ገነት አሠፋ በነሐሴ ወር 1997 ዓ.ም በተለያዩ ቀናት በመ/ቤቱ በተለመደው አሠራር መሠረት በሥራ መግቢያና መውጫ ሰዓት በሰዓት ፊርማ መቆጣጠሪያ ደብተር ላይ በቀን አራት ጊዜ እየፈረመች በመደበኛ የሥራ ገበታዋ ላይ ተገኝታ እያለ የግል ተበዳይዋን ፊርማ በፍሉድ ደልዞ በማጥፋት በሥራዋ ላይ ያልተገኘች ለማስመሰል እና በህክምና ፈቃድ ምክንያት በሥራ ገበታዋ ላይ ባልተገኘባቸው ቀናት የመንግሥትን የሥራ ሰዓት እንዳባከነች የሚገልጽ ሀሰተኛ ሰነድ አዘጋጅቷል፡፡ ይህንም ምክንያት በማድረግ በሥልጣኑ ያለአግባብ በመገልገል ከመስከረም ወር 1998 ዓ.ም የግል ተበዳይ ደመወዝ ላይ የ7 ቀን ተኩል ክፍያ ተቀንሶ ለመንግሥት ገቢ እንዲሆን በማድረግ በግል ተበዳይዋ መብት እና ጥቅም ላይ ጉዳት አድርሷል፡፡ ተከሳሹ በኮሚሽኑ የቀረበበትን የሰውና የሰነድ ማስረጃ ሊከላከል ባለመቻሉ እና በሁለቱም የሙስና ወንጀሎች ጥፋተኛ ሆኖ በመገኘቱ ፍርድ ቤቱ ከዚህ በላይ በተጠቀሰው ቀን በዋለው ችሎት እጁ ከተያዘበት ጊዜ ጀምሮ በሁለት ዓመት ከስድስት ወር እስራት እንዲቀጣ ወስኖበታል፡፡ |
|
ኮሚሽኑ ህብረተሰቡን በፀረ-ሙስና ትግሉ ውስጥ ለማሳተፍ እየተንቀሳቀሰ ነው አዲስ አበባ (ኢዜአ)፡- የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ህብረተሰቡን በፀረ-ሙስና ትግሉ ውስጥ ማሳተፍ የሚያስችል ሥርዓት ዘርግቶ በስፋት እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ዓለም አቀፉን የፀረ-ሙስና ቀን ምክንያት በማድረግ ኮሚሽኑ ታህሳስ 4 ቀን 2001 ዓ.ም ባዘጋጀው ሕዝባዊ ስብሰባ ላይ ኮሚሽነር አቶ አሊ ሱለይማን እንዳስታወቁት፤ ኮሚሽኑ ህብረተሰቡ በፀረ-ሙስና ትግሉ ውስጥ የነቃ ተሳትፎ እንዲኖረው በስፋት ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡ ህብረተሰቡ የሙስና ድርጊቶችን በማጋለጥና በመጠቆም፣ ከሙሰኞች ጋር ባለመተባበር፣ መልካም ሥነምግባርን በመከተልና በማስፋፋት ሙስናን በጽናት እንዲታገልም አሳስበዋል፡፡ ሙስና እና ኢ-ሥነምግባራዊ ድርጊቶች የሚፈፀሙት በህብረተሰቡ ውስጥ መሆኑን ያመለከቱት ኮሚሽነሩ፤ ችግሮቹ በህብረተሰቡ ውስጥ እስካሉ ድረስ መፍትሄዎቹ ከህብረተሰቡ እንደማይርቁም ገልፀዋል፡፡ የፀረ-ሙስና ትግሉ በሕዝባዊ መሠረት ላይ ካልቆመ የሚፈለውን ውጤት ማስመዝገብ አይቻልም፣ መላው ሕዝብ ያልተሳተፈበት የፀረ-ሙስና ትግልም ግቡን አይመታም ብለዋል፡፡ የውይይቱ ዓላማ ኮሚሽኑ የሚያደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች ለህብረተሰቡ ለማስገንዘብና ለፀረ-ሙስና ትግሉ የሚረዱ አዳዲስ ሃሳቦችን ለማግኘት እንዲሁም በፀረ-ሙስና ትግሉ ውስጥ ህብረተሰቡ የድርሻውን እንዲወጣ ለማስቻል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን የሥነምግባር ትምህርት እና ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ አሰፋ በበኩላቸው ኮሚሽኑ ከተቋቋመ ወዲህ ሙስና በሀገሪቱ ሊያስከትል የሚችለውን ጥፋት ህብረተሰቡ እንዲረዳ ጥረት ማድጉን ገልጸዋል፡፡ ኮሚሽኑ ባለፈው በጀት ዓመት ከሙስና ጋር ግንኙነት ያላቸውን ጨምሮ ሌሎች ሦስት ሺ ጥቆማዎችን መቀበሉን ያስታወሱት ዳይሬክተሩ፤ ወደፊትም የህብረተሰቡ ተሳትፎ አሁንም በከፍተኛ ደረጃ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ ባለፈው በጀት ዓመት በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የመሬት ወረራ መካሄዱን ጠቁመው 6ዐዐ ሺህ ካሬ ሜትር መሬት በሕግ እንዲታገድ ማድረጉንም አስታውሰዋል፡፡ |
|
ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን በኮሚሽኑ ሠራተኞች ተከበረ በየዓመቱ እ.ኤ.አ ከ2ዐዐ3 ጀምሮ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅቶት ጠቅላላ ጉባዔ ውሳኔ መሠረት በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ5ኛ ጊዜ በአገራችን ደግሞ ለ4ኛ ጊዜ የሚከበረውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን አስመልክቶ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሠራተኞች ቀኑን በተለያዩ ዝግጅቶች አከበሩ፡፡ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀረ-ሙስና ኮንቬንሽን ለመጀመሪያ ጊዜ ከዲሴምበር 9-11 ቀን 2ዐዐ3 በሜክሲኮ-ሜሪዳ ከተማ ለአባል አገራት ፊርማ የቀረበበትን ቀን ለማስታወስ በየዓመቱ ዲሴምበር 9 ቀን ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን ሆኖ እንዲከበር በመንግሥታቱ ድርጅት በተወሰነው መሠረት ዘንድሮ ዕለቱ በአገራችን የሚከበረው ‹‹ሙስናን በፅናት በመዋጋት መልካም አስተዳደርን እናረጋግጥ›› በሚል መሪ ሐሳብ ነው፡፡ የኮሚሽኑ ሠራተኞች ሕዳር 3ዐ ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም (ዲሴምበር 9 ቀን 2ዐዐ8) በዓሉን ለማክበር በኮሚሽኑ የስብሰባ አዳራሽ ባደረጉት የግማሽ ቀን ስብሰባ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለፀረ-ሙስና ትግሉ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚኖራቸው የታመኑና በፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ተግባራዊ እየሆኑ የሚገኙ እንቅስቃሴዎችን የተመለከቱ ማብራሪያዎች በተለያዩ የሥራ ኃላፊዎች ቀርበዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ከሰባት ዓመታት በኋላ እ.ኤ.አ በ2ዐዐ9 ሁለተኛው የሙስና ቅኝት በአገር አቀፍ ደረጃ እንደሚካሄድ ተገልጿል፡፡ ከዓለም ባንክ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ የሚካሄደው የሙስና ቅኝት በአገራችን የፀረ-ሙስና ተቋማት ከተቋቋሙ በኋላ ሕብረተሰቡ በሙስና ላይ ያለውን አመለካከት ለማወቅ የሚረዳ ነው፡፡ የጥናቱ ውጤትም ምን ዓይነት ሙስና፣ በየት አካባቢ እና በምን ደረጃ እንደሚገኝ ለመረዳት ስለሚያስችል በዚህ ዙሪያ በተለያዩ አካላት ለሚቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የሚረዳ ከመሆኑም በላይ በፀረ-ሙስና ትግሉ ኮሚሽኑ ሊከተለው የሚገባውን አቅጣጫ ለመተለም የሚያስችል ነው፡፡ በተመሳሳይም በተወካዮች ምክር ቤት ወደፊት እንደሚፀድቅ ስለሚጠበቀው የሀብትና የገንዘብ ጥቅሞች ምዝገባ ረቂቅ አዋጅን የተመለከተ ማብራሪያ በኮሚሽኑ የሕግ ባለሙያ ቀርቧል፡፡ ኮሚሽኑ በ1999 በጀት ዓመት ያካሄደውን መሠረታዊ የአሠራር ሥርዓት ጥናት ተከትሎ በአዲስ መልክ ተደራጀው የሥነምግባር አውታሮች ማስተባበሪያ መምሪያ ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ያደረጋቸውን እንቅስቃሴዎች የተመለከተ ማብራሪያ የተሰጠ ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የኮሚሽኑ ተገልጋዮች በኮሚሽኑ አሠራር ላይ ያላቸውን እርካታ በተመለከተ በ2ዐዐዐ ዓ.ም በተካሄደው የሁለተኛ ዙር የመሠረታዊ የቅኝት ጥናት ውጤት (baseline survey) ላይ ማብራሪያዎች ተሰጥተዋል፡፡ በመጨረሻም በአገራችን ለ4ኛ ጊዜ በዓለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ5ኛ ጊዜ የሚከበረውን ይህን በዓል አስመልክቶ በኮሚሽኑ ሠራተኞች ለውድድር ከቀረቡ ግጥሞች መካከል ከ1ኛ-3ኛ የወጡ ግጥሞች ቀርበው በመድረክ ላይ የተነበቡ ሲሆን ለአሸናፊዎቹም ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ በዓሉን አስመልክቶ ሌሎችም ተከታታይ ዝግጅቶች እንደሚካሄዱ የታወቁ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ ታህሳስ 4 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም በመንገድ ትራንስፖርት ባለሥልጣን የስብሰባ አዳራሽ 300 ያህል ተጋባዥ እንግዶች የሚገኙበት ሕዝባዊ ስብሰባ እና ታህሳስ 12 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም ደግሞ በመስቀል አደባባይ የማካሄድ የብስክሌት ውድድር እንደሚገኝበት ታውቋል፡፡ |
|
የዘንድሮው ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ጥረት በሚደረግበት ጊዜ መከበሩ ልዩ እንደሚያደርገው ተገለጸ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ5ኛ ጊዜ በአገራችን ደግሞ ለ4ኛ ጊዜ ሕዳር 3ዐ ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም የተከበረው ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን ከልማት ጥረታችን በተጨማሪ መንግሥታችን መልካም አስተዳደርን ለማስፈን በሚንቀሳቀስበት ጊዜ የሚከበር በመሆኑ ዕለቱን ልዩ እንደሚያደርገው የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ክቡር አቶ አሊ ሱለይማን ገለፁ፡፡ ክቡር ኮሚሽነሩ ይህን የገለፁት ሕዳር 26 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም በኪሚሽኑ የስብሰባ አዳራሽ በበዓሉ አከባበር እና በኮሚሽኑ የሥራ እንቅስቃሴ ዙሪያ ለተለያዩ የመንግሥት የመገናኛ ብዙኃን ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ወቅት ነው፡፡ እንደክቡር ኮሚሽነሩ ማብብሪያ ባለፉት ሰባት ዓመታት ኮሚሽኑ እና አጋር ድርጅቶች ባደረጉት ጥረት በአገራችን ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ሙስናን የመነጋገሪያ አጀንዳ ከማድረግ አልፈው በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴው ውስጥ ንቁ ተሳታፊ ለመሆን ችለዋል፡፡ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አባል አገሮች ከሦስት ዓመት ላላነሰ ጊዜ በመረቀቅ ሂደት ውስጥ ያለፈው የተባበሩት መንግሥታት የፀረ-ሙስና ኮንቬንሽን ለአባል አገሮች ፊርማ የቀረበበትን ዕለት እ.ኤ.አ ዲሴምበር 9 ቀን 2ዐዐ3 ምክንያት በማድረግ በአገራችን የሚከበረው የዘንድሮው ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን የኢፌዴሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተባበሩት መንግሥታትን የፀረ-ሙስና ኮንቬንሽንና የአፍሪካ ሕብረትን የሙስና መከላከያ እና መዋጊያ ስምምነት ባፀደቀበት ማግስት የሚከበር በመሆኑ ልዩ ቦታ እንደሚሰጠው ክቡር ኮሚሽነሩ አክለው ገልፀዋል፡፡ የተባበሩት መንግሥታት የፀረ-ሙስና ኮንቬንሽን በብሔራዊም ሆነ በዓለም አቀፉ ደረጃ ሙስናን ለመዋጋት እንዲሁም በአባል አገሮች ዘንድ የተቀናጀ እና የትብብር ስራ ለማከናወነ እጅግ ጠቃሚ ከመሆኑም በላይ በሙስና የተዘረፈንና ከአንድ አገር ወደሌላ አገር የተሸጋገረ ሐብትን በማስመለስ ሙስና ፈጻሚዎችን ተጠያቂ ለማድረግ ስምምነቱ ከፍተኛ ድጋፍ እንደሚያደርግም አስገንዝበዋል፡፡ የዘንድሮው ዓለም አቀፍ የፀረ-ሙስና ቀን አገራችን በልማቱ መስክ ፈጣን እድገት እያስመዘገበች ባለችበት ወቅት እንዲሁም ሙስና የልማታችን እና የእድገታችን እንቅፋት እንዳይሆን ከሙስና የፀዳች ኢትዮጵያን በጋራ ጥረት የመገንባት ራዕይ ይዘን የምናከብረው ከመሆኑም በላይ መንግሥት ለፀረ-ሙስና ትግሉ አጋዥ የሆኑ ልዩ ልዩ ሕጐችን ለማውጣት እየተንቀሳቀሰ ባለበት ወቅት መከበሩም የተለየ ስሜት እንደሚሰጥ ተመልክቷል፡፡ ክቡር ኮሚሽነሩ የኮሚሽኑን የሥራ እንቅስቃሴ አስመልክተውም የሥነምግባር ትምሕርትን በማስፋፋት እና በማስረጽ፣ በሕግ ማስከበር እንቅስቃሴ፣ በሙስና መከላከል፣ የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴውን በሚያግዙና አዲስ እንደሚወጡ በሚጠበቁ አዋጆች ዙሪያ እንዲሁም በፌደራል እና በክልል ከሚገኙ የሥነምግባር አውታሮች ጋር ስላለው የትብብር እና የመደጋገፍ ሥራ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በዓለም ባንክ ድጋፍ ሁለተኛውን የፀረ-ሙስና ቅኝት ለማካሄድ የሚያስችል ቅድመ ዝግጅት ተደርጐ እ.ኤ.አ በ2ዐዐ9 ጥናቱን የማካሄድ ሥራ እንደሚከናወን የገለፁት ክቡር ኮሚሽነሩ፣ የአገራችንን የፀረ-ሙስና ትግል የተሻለ አቅጣጫ ለማስያዝ የሚረዳ የፀረ-ሙስና ፖሊሲ ረቂቅ ተዘጋጅቶ አስተያየት እየተሰጠበት እና እየዳበረ እንደሚገኝም አስገንዝበዋል፡፡ በተመሳሳይም የዓለም ባንክ በአገራችን በሚካሄዱ የኮንስትራክሽን ሥራዎች ላይ ባካሄደውና እ.ኤ.አ በጁን 2ዐዐ8 ይፋ ያደረገውን የጥናት ውጤት አስመልክተውም በሌሎች አገሮች ከተካሄደው የጥናት ውጤት አንፃር በአገራችን በዘርፉ አነስተኛ የሙስና መጠን እንደሚስተዋል ገልፀው፣ ይህም ሆኖ የኮንስትራክሽን ሥራ ጥራት ማነስ፣ የተጋነነ ዋጋ፣ ለጥገና ተገቢውን ትኩረት አለመስጠት፣ ሙያዊ ብቃትን በማስከበርና በመሳሰሉት ጥንቃቄ ሊደረግባቸው የሚገቡ የዘርፉ ችግሮች መሆናቸውን ጥናቱ እንደሚያመለክት አስምረውበታል፡፡ |
|
ኮሚሽኑ እና የብዙኃን ማሕበራት የጋራ የትብብር እና የምክክር መድረክ መሰረቱ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እና 15 የብዙኃን ማሕበራት በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ በቅንጅት ሊሰሩ የሚያስችላቸውን ቋሚ የትብብርና የጋራ የምክክር መድረክ ሕዳር 24 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም በኢምፔሪያል ሆቴል ባካሄዱት ስብሰባ መሠረቱ፡፡ በኮሚሽኑ እና በብዙኃን ማሕበራት መካከል የተመሠረተው ቋሚ የትብብርና የጋራ የምክክር መድረክ ዓላማ የብዙኃን ማሕበራት አባሎቻቸውን በመልካም ሥነምግባር በማነጽ ጠንካራ የፀረ-ሙስና ትግል እንዲያደርጉ በማስቻል ሙስናን የሚጠየፍና በብቃት የሚዋጋ ሕብረተሰብ ለመገንባት የሚደረገውን ትግል ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ ነው፡፡ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ክቡር አቶ አዲሱ መንግሥቱ በጋራ የምክክር መድረኩ መመስረቻ ስብሰባ መክፈቻ ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር የብዙኃን ማሕበራት ሙስናን በመዋጋት እና በመከላከል ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱ ገልፀው፣ እነርሱ ያልተሳተፉበት የፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ ውጤታማነቱ አጠራጣሪ ነው በሚባልበት ዓለም አቀፍ ሁኔታ ውስጥ እንደምንገኝ አስረድተዋል፡፡ በፀረ-ሙስና ትግሉ የብዙኃን ማሕበራት ተፈላጊ የሚያደርጋቸው ከፖለቲካ ወገንተኝነት የራቁ ናቸው ተብለው ስለሚታመኑ ከሕብረተሰቡ ጋር ቅርበት ያላቸውና ለሕብረተሰቡ ጥቅም ይሰራሉ ተብሎ ስለሚወሰድ ነው ያሉት ምክትል ኮሚሽነሩ፣ ማሕበራቱ በፀረ-ሙስና እንቅስቃሴ ውስጥ በንቃት ከተሳተፉ ከመንግሥት ተቋማት ባልተናነሰ መልኩ ውጤታማ ሊሆኑ ስለሚችሉ በፀረ-ሙስና ትግሉ ውስጥ ተመራጭ እንደሚያደርጋቸው ገልፀዋል፡፡ ምክትል ኮሚሽነሩ አክለውም የብዙኃን ማሕበራት ከሕብረተሰቡ ተአማኒነትን ለማግኘትና አባላቱም ከእነርሱ ተገቢውን አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ እውን እንዲሆን የአባላትን መብትና ጥቅም በከፍተኛ ደረጃ ከሚጐዱ ተግባራት ቀዳሚው ሙስና በመሆኑ በፀረ-ሙስና ትግሉ ከእነርሱ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚጠበቅ ተገንዘበው በዚህ ዙሪያ ከኮሚሽኑ ጋር እጅና ጓንት ሆነው በመንቀሳቀስ ሙስናን ለመዋጋት በሚደረገው ጥረት ከመቸውም ጊዜ በላይ ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉ አሳስበዋል፡፡ በዕለቱ በተካሄደው ስብሰባም በኮሚሽኑ እና በብዙኃን ማሕበራት የትብብር እና የምክክር የጋራ መድረክ የመመስረቻና የሥራ መመሪያ የመጨረሻ ረቂቅ ላይ በኮሚሽኑ የሥነምግባር አውታሮች ማስተባበሪያ መምሪያ ዳይሬክተር አማካኝነት ማብራሪያ ከቀረበና በረቂቁ ላይ ሰፊ ውይይት ከተካሄደ በኋላ በተወሰኑ አንቀጾች ላይ ማሻሻያዎች ተደርገው መመሪያው ፀድቋል፡፡ በመመሪያው ላይ የትብብር እና የምክክር ቋሚ መድረኩ ሰብሳቢ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን እንዲሆን የተደነገገ ሲሆን፣ ምክትል ሰብሳቢው ከአባል ማሕበራት እንዲመረጥ በተወሰነው መሠረት ኃላፊነቱን የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማሕበራት ኮንፌዴሬሽን ለሁለት ዓመታት እንዲይዝ ተመርጧል፡፡ ከትብብር እና የምክክር የጋራ መድረኩ ምስረታ በኋላ በጋራ መድረኩ ቀጣይ ተግባራት ላይ ለመወያየት የብዙኃን ማሕበራቱ ተወካዮች በኮሚሽኑ ወደፊት ጥሪ እንደሚደረግላቸው በስበሰባው ማጠቃለያ ላይ ተገልጿል፡፡ |
|
ለትምህርት ቤት የሥነምግባር ክበባት የአመራር አካላት የተዘጋጀ የአሰልጣኞች ሥልጠና ተሰጠ አዲስ አበባ/ፌሥፀኮ/ የአዲስ አበባን እና የድሬዳዋ አስተዳደርን ጨምሮ ከሁሉም ክልሎች ለተውጣጡ 69 የትምሕርት ቤት የሥነምግባር እና ሥነዜጋ ክበባት አመራር አካላት የተዘጋጀ የአሰልጣኞች ሥልጠና ተሰጠ፡፡ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያዘጋጀውና ከሕዳር 15-16 ቀን 2001 ዓ.ም በኮሚሽኑ አዳራሽ የተካሄደው የአሰልጣኞች ሥልጠና ዓላማ ሠልጣኞቹ ተወክለው በመጡባቸው ት/ቤቶች የሚገኙ የሥነምግባር እና ሥነዜጋ ክበባት አባላትን በመመዝገብ እና የፋይናንስ ምንጮችን በማፈላለግ ክበባቱ የሚጠናከሩበትን መንገድ እንዲያመቻቹ እና በመልካም ሥነምግባር እና በሙስና ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምሕርት ለሌሎች ለማስተላለፍ የሚያስችላቸውን አቅም እንዲፈጥሩ ለማስቻል እንደሆነ ከሥልጠናው አዘጋጆች ተገልጿል፡፡
በሥልጠናው ላይ
የሥነምግባር እና የሙስና ጽንሰ ሐሳብ እንዲሁም የሥነምግባር ትምሕርት አስፈላጊነትና የክበባት አደረጃጀት ሚና በሚሉ
ርዕሶች ዙሪያ ማብራሪያዎች የቀረቡ ሲሆን የት/ቤት የሥነምግባር እና የሥነዜጋ ክበባት በሚጠናከሩበት ሁኔታ ላይ
የተካሔዱ የቡድን ሥራዎች በሥልጠናው ተሳታፊዎች ቀርበው ውይይት ተደርጐባቸዋል፡፡ |
|
የቴሌኮሙኒኮሽን
መሣሪያ በሕገወጥ
መንገድ ሲጠቀሙ
ተገኝተዋል የተባሉ
ተጠርጣሪዎች
በቁጥጥር ስር ዋሉ የፌደራል
የሥነምግባር እና
የፀረ-ሙስና ኮሚሽን
ወደ ኢትዮጵያ
እንዳይገባ
የተከለከለና አገር
ውስጥና ወደ ውጭ
ሀገር ለመደወልና
ጥሪ ለመቀበል
የሚያገለግል የቴሌ
ኮሙኒኬሽን መሣሪያ
ሲጠቀሙ የተገኙ
ስምንት
ተጠርጣሪዎች
በቁጥጥር ስር
መዋላቸውን
አስታወቀ፡፡ በኮሚሽኑ
የሥነምግባር
ትምህርት እና
የሕዝብ ግንኙነት
መምሪያ ዳይሬክተር
አቶ ብርሃኑ አሰፋ
ህዳር 12 ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም
እንዳስታወቁት፣
ተጠርጣሪዎቹ
በቁጥጥር ሥር
የዋሉት ከህዳር 1ዐ
እስከ ህዳር 12 ቀን
2ዐዐ1 ዓ.ም ባሉት
ቀናት ነው፡፡ በቁጥጥር
ሥር ሊውሉ የቻሉትም
በሀገር ደህንነት
ላይ አደጋ ሊደቅን
በሚችል ሕገወጥ
ተግባር ውስጥ
ተሳትፈዋል በሚል
ተጠርጥረው
እንደሆነ
ገልፀዋል፡፡ ድርጊቱም
በኢትዮጵያ ቴሌ
ኮሙኒኬሽን
ኮርፖሬሽን
አማካኝነት ለአገር
ይገባ የነበረውን
ገቢ በሕገወጥ
መንገድ ወደ
ተጠርጣሪዎቹ ኪስ
እንዲገባ ሆኗል
በሚል በቁጥጥር ሥር
መዋላቸውን
ጠቁመዋል፡፡ በቁጥጥር
ሥር ከዋሉት መካከል
አንዱ ግለሰብ
በአምስት ቦታዎችና
በተለያዩ ስሞች
ድርጊቱን ይፈጽም
እንደነበር
ታውቋልዋ
ብለዋል፡፡ አራቱ
ደግሞ በቀጥታ
ከድርጊቱ ጋር
ግንኙነት ያላቸውና
ዋነኛ ተዋናዮች
መሆናቸውን
ጠቅሰው፣ ቀሪዎቹ
ከድርጊቱ ጋር
ግንኙነት አላቸው
በሚል በቁጥጥር ሥር
መዋቸውን
አብራርተዋል፡፡ በቁጥጥር
ስር ከዋሉት
ተጠርጣሪዎች
መካከል አንዱ የውጭ
ዜጋ መሆኑን
የሚያመለክቱ
መረጃዎች
መገኘታቸውንም
ገልፀዋል፡፡ ይህም
የሀገርን ደህንነት
አደጋ ላይ ሊጥል
የሚችል መሆኑን
ጠቁመዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ
ሲጠቀሙባቸው
የነበሩ ሕገወጥ
መሣሪያዎች፣
መስመሮችና ሌሎች
ለጥሪ አገልግሎት
የሚውሉ መሣሪያዎች
በፍተሻ
መያዛቸውንም
አስታውቀዋል፡፡ ከወንጀሎቹ
መካከልም በቦሌ
ክፍለ ከተማ አራት፣
በአራዳ ክፍለ ከተማ
ሁለት፣ በቂርቆስ
ክፍለ ከተማ በአንድ
ስፍራ ላይ
በኢንተርኔት፣
በኮምፒዩተር
ማሠልጠኛ እና በልዩ
ልዩ ቢሮዎች ሽፋን
ድርጊቶቹ ሲፈፀሙ
መቆየታቸውን
ዳይሬክተሩ
አብራርተዋል፡፡ ይህም
የቴሌኮሙኒኬሽን
አገልግሎትን
ለማስፋፋት
በሚደረገው ጥረት
ላይ ተጽዕኖ
የሚያደርግ መሆኑን
ጠቅሰው፤ የሀገርን
ደህንነት የሚጐዳ
በመሆኑን
ሕብረተሰቡ
የድርጊቱን
ፈፃሚዎች በማጋለጥ
ሊሳተፍ እንደሚገባ
አስገንዝበዋል፡፡ በዚህ
ሕገወጥ ድርጊት
እጃቸው አለበት
የተባሉ ሌሎች
ተጠርጣሪዎችንም
በቁጥጥር ሥር
ለማዋል ክትትሉ
አሁንም እንደቀጠለ
ነው ብለዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ ከትናትን በስቲያ በፌዴራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አንደኛ ወንጀል ችሎት መቅረባቸውን ጠቁመው ኮሚሽኑ ለተጨማሪ ምርመራ የጊዜ ቀጠሮ በጠየቀው መሠረት የ14 ቀን ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ በፍርድ ቤቱ እንደተፈቀደለት ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል፡፡ |
|
ኮሚሽኑ
እና 22 የሙያ
ማህበራት የጋራ
የትብብር እና
የምክክር መድረክ
መሠረቱ የፌደራል
የሥነምግባር እና
የፀረ-ሙስና ኮሚሽን
እና 22 የሙያ
ማሕበራት ሕዳር 12
ቀን 2ዐዐ1 ዓ.ም
በሂልተን ሆቴል
ባካሄዱት ስብሰባ
የጋራ የትብብር እና
የምክክር መድረክ
መሰረቱ፡፡ የጋራ
የትብብር እና
የምክክር መድረኩ
ዓላማ ኮሚሽኑ እና
የሙያ ማሕበራት
በመካከላቸው
ጠንካራ የትብብር
ግንኙነት በመፍጠር
ሙስናን ሊሸከም
የማይችል
ሕብረተሰብ
ለመገንባት
በሚደረግ ትግል
አስፈላጊውን
አስተዋጽኦ
እንዲያበረክቱ
ለማስቻል እና
አባላቱ እርስ
በእርሳቸው
በመመካከር፣
በመደጋገፍ፣ ልምድ
በመለዋወጥና
በመረዳዳት
የመፈፀም
አቅማቸውን
ለማሳደግና ጠንካራ
የፀረ-ሙስና አቋም
እንዲኖራቸው
ለማስቻል ነው፡፡ በስብሰባው
ላይ የፌደራል
የሥነምግባር እና
የፀረ-ሙስና ኮሚሽን
ኮሚሽነር ክቡር አቶ
አሊ ሱለይማን
ባደረጉት የመክፈቻ
ንግግር ሁሉም
ባለሙያዎች በየሙያ
ዘርፋቸው ያለውን
የሙያ ሥነምግባር
ጠብቀው ሕዝቡን
ማገልገል ቅድሚያ
ትኩረት ሊሰጡት
የሚገባ ተግባር
መሆኑን
ገልፀዋል፡፡
በየትኛውም የሙያ
ዘርፍ
የሥነምግባሮች ሁሉ
ቁንጮ ሐቀኝነት
መሆኑን የገለፁት
ኮሚሽነሩ፣ ይህ
ደግሞ ከሙስና አና
ከብልሹ አሠራር
መራቅ ማለት መሆኑን
አስረድተዋል፡፡ ኮሚሽነሩ
አክውም
ከሕብረተሰቡ
ተዓማኒነትን
ለማግኘትና
ሕብረተሰቡም
ከሙያቸው ተገቢውን
አገልግሎት
እንዲያገኝ የሙያ
ማሕበራት
ከሚከተሉት የሙያ
ሥነምግባር
በተፃራሪ በሚቆም
ባለሙያ ላይ
የራሳቸውን እርምጃ
የሚወስዱበትን
ሥርዓት መዘርጋት
የግድ እንደሚልም
ገልፀዋል፡፡ የሙያ
ማሕበራቱ ይህን
የሙያ
ሥነምግባራቸውን
በዘላቂነት
ለማስጠበቅ
ጠንክረው
የሚሰሩበት ሁኔታ
ካለ ደግሞ ለሙያው
ባለቤቶች
የራሳቸውን የሙያ
ፈቃድ የሚሰጡበትና
ራሳቸውን በራሳቸው
የሚያስተዳድሩበት
ጊዜ ሩቅ
እንደማይሆን
ያላቸውን እምነት
ገልፀዋል፡፡ በስብሰባው
ላይ ሙስናን
በመከላከል የሙያ
ማሕበራት ሚና
በሚል ርዕስ
የተዘጋጀ ጥናታዊ
ጽሁፍ በኮሚሽኑ
ምክትል ኮሚሽነር
በክቡር አቶ አዲሱ
መንግሥቱ የቀረበ
ሲሆን በጥናታዊ
ጽሁፍ ላይ የሙያ
ማሕበራት በራሳቸው
ሙያ የሚከሰትን
ሙስና ከመዋጋት
በተጨማሪ በአገራዊ
የፀረ-ሙስና ትግሉ
ሊያበረክቱ
ስለሚችሉት
አስተዋጽኦ
ማብራሪያ
ሰጥተዋል፡፡ በመጨረሻም
የኮሚሽኑ የሥራ
ኃላፊዎችና የየሙያ
ማሕበራቱ ተወካዮች
በጋራ የትብብርና
የምክክር መድረኩ
ረቂቅ የማቋቋሚያና
የሥራ መመሪያ ላይ
ተወያይተው
የተወሰኑ
ማስተካከያዎችን
በማድረግ
አፅድቀውታል፡፡ በጋራ መድረኩ ማቋቋሚያ እና የሥራ መመሪያ መሠረት የጋራ መድረኩ ሰብሳቢ የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሲሆን ለሁለት ዓመታት የሚቆየውን የምክትል ሰብሳቢነት የሥራ ድርሻ ደግሞ የኢትዮጵያ መምሕራን ማሕበር እንዲረከብ በዕለቱ ተመርጧል፡፡ |
|
13.5
ሚሊዮን
ብር የሚገመት መሬት
በህገወጥ መንገድ
የሰጡ በእስራት እና
በገንዘብ ተቀጡ
አዲስ
አበባ ፡- (ፌ.ስ.ፀ.ኮ)
ጥቅምት 27/2001 ዓ.ም
የፌደራል ከፍተኛ
ፍ/ቤት አንደኛ
ወንጀል ችሎት
በኮንዶሚኒየም
አደረጃጀት ደንብ
መሠረት ላልተደራጁ
ግለሰቦች በህገወጥ
መንገድ የግንባታ
ቦታ ሰጥተዋል የሚል
ክስ
የተመሰረተባቸው 5
ግለሰቦች ከ1 ዓመት
ከ6 ወር እስከ 10 ዓመት
በሚደርስ ጽኑ
እስራት እና
በገንዘብ እንዲቀጡ
ወሰነ፡፡ የፌደራል
የሥነምግባር እና
የፀረ-ሙስና ኮሚሽን
በነክፍሌ እሸቴ
መዝገብ በአምስት
ግለሰቦች ላይ
የመሰረተው ክስ
ተከሳሾቹ በጉለሌ
ክ/ከተማ የሚገኝ ከ27,000
ካሬ ሜትር በላይ
የሆነን መሬት በህገ
ወጥ መንገድ
ለግለሰቦች
መስጠታቸውን
ያመለክታል፡፡ በኮንዶሚኒየም
አደረጃጀት ደንብ
መሠረት
ላልተደራጁት
ግለሰቦች በህገወጥ
መንገድ የተሰጠው
መሬት የሊዝ ዋጋ
ግምቱ ከ13.5 ሚሊዮን
ብር በላይ መሆኑም
ተገልጿል፡፡ ተከሳሾቹ
በተመሰረተባቸው
የሙስና ወንጀል ክስ
ጥፋተኛ ሆነው
በመገኘታቸው ፍ/ቤቱ
ጥቅምት 26/2001 ዓ.ም
በዋለው ችሎት
የጉለሌ ክ/ከተማ
የመሬት ልማት ቡድን
መሪ እና መሐንዲስ
የነበረው 1ኛ
ተከሳሽ ክፍሌ እሸቴ
ከዚህ ቀደም በሌላ
ፋይል የተቀጣው
ተደምሮ በ9 ዓመት
ጽኑ እስራት እና 2,500
ብር እንዲቀጣ
ወስኗል፡፡ በክፍለ
ከተማው የቦታና
የቤት ውል
ማስፈፀሚያ ሐላፊ
የነበረው 2ኛ
ተከሳሽ ሽፈራው
አስገዶም ደግሞ በ1
ዓመት ከ6 ወር ጽኑ
እስራት እንዲቀጣ
ተወስኖበታል፡፡ የመሬት
ይዞታ ውል ምዝገባ
ኦፊሰር የነበረው
3ኛ ተከሳሽ ታረቀ
ኑርጊ ከዚህ በፊት
የተቀጣው ታስቦ በ10
ዓመት ጽኑ እስራት
እና 2,500 ብር እንዲቀጣ
ፍ/ቤቱ ወስኗል፡፡ በዚሁ
መዝገብ ክስ
የተመሰረተበትና
በክፍለ ከተማው
ይዞታ ቅየሳ ባለሙያ
የነበረው 4ኛ
ተከሳሽ ደሳለኝ
አባተ በ8 ዓመት ጽኑ
እስራት እና 2000 ብር፣
የማህበራት
ማከፋፈያ ተጠባባቂ
ቡድን መሪ የነበረው
እና በ5ኛ ደረጃ
ተከሳሽነት
የቀረበው ምስጋናው
ሰኢድ ደግሞ በ2
ዓመት ጽኑ እስራት
እንዲቀጡ ፍ/ቤቱ
ወስኗል፡፡ |
|
የሙስና
ወንጀል የፈፀሙ በ6
ዓመት እስራት እና
በገንዘብ ተቀጡ አዲስ
አበባ፡- ፌ.ሥ.ፀ.ኮ የፌደራል
ከፍተኛ ፍ/ቤት
የድሬዳዋ ምድብ
ችሎት የፌደራል
የሥነምግባር እና
ፀረ-ሙስና ኮሚሽን
በሥራ ላይ በሚፈፀም
የመውሰድና
የመሰወር ወንጀል
ክስ የመሠረተባቸው
እነ ምክትል ሣጅን
መሐመድ ሁሴን
አምስት ግለሰቦች
እያንዳንዳቸው በ6
ዓመት ጽኑ እሥራት
እና 3000 ብር እንዲቀጡ
ወሰነ፡፡ |